1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

መራዘም ያልታከተዉ የኢትዮጵያ የግብፅና የሱዳን ውይይት

Merga Yonas Bulaሰኞ፣ ጥቅምት 15 2008

ኢትዮጵያ በምትገነባዉ ግዙፍ የኃይል ማመንጫ ግድብ ሰበብ ሦስቱ ሃገራት በተለያዩ ጊዜያት ዉይይት ሲያካሂዱ ቆይተዋል። ከካይሮ የወጡ አንዳንድ ዘገባዎች እንደሚጠቁሙት ግድቡን ለማጥናት ከተሰየሙ የዉጭ ኩባንያዎች አንዱ ከጥናቱ ራሱን ካገለለ በኋላ ግብፅ ግድቡን በተመለከተ ታሰማዉ የነበረዉ ሥጋት አይሏል።

https://p.dw.com/p/1GuYo
Äthiopien Grand Renaissance Staudamm al-Sisi al-Bashir Desalegn
ምስል Ashraf Shazly/AFP/Getty Images

[No title]

የኢትዮጵያ ግብፅና ሱዳን የጋራ የቴክኒክ ኮሚቴ ስብሰባ እንደ አውሮፓውያኑ ጥቅምት ወር መጨረሻ ወይም ኅዳር መጀመርያ` ላይ በካይሮ ለማካሄድ ድጋሚ እንደታቀደ ተጠቆመ።


እ.ኤ.አ. ጥቅምት 5 ቀን 2015 ላይ የሶስትዬዎሹ የጋራ የቴክኒክ ኮሚቴ ስብሰባ ለማካሄድ ቢታቀደም፣ በኢትዮጵያ በኩል በመንግሥት ምሥረታ ምክንያት ጊዜዉ እንዲራዘም ጥያቄ በመቅረቡ ለሁለት ሳምንት እንዲገፋ መደረጉን ዘገባዎች ያሳያሉ። በዚህ መሠረትም ስብሰባዉን በአውሮጳውያኑ ጥቅምት ወር መጨረሻ ወይም ኅዳር መጀመርያ ገደማ ለማካሄድ እንደታቀደ በዉሃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር የወሰን ተሻጋሪ ወንዞች ጉዳይ ዳይሬክተር የሆኑት ኢንጅነር ተሾመ ኣጥናፌ ለዶቼ ቬሌ ተናግርዋል።


ስብሰባዉን ማራዘም ያስፈለገበት ምክንያት ኢትዮጵያን ጨምሮ ሌሎች የአባይ ተፋሰስ ኢኒሼቲቭ ኢጋድና ሌሎችም ስብሰባ ሰለነበራቸዉ ነዉ እንጅ በኢትዮጵያ በኩል ያለ ችግር አይደለም ይላሉ አቶ ተሾመ። ስብሰባዉን ለማድረግ ሰብሳቢ ኮሚቴዎች አሁን ዉይይት እያደረጉ መሆኑን በመጥቀስም፣ በሚቀጥለዉ 15 ቀናት ዉሰጥ ስበሰባዉ ይካሄዳል ተብሎ እንደሚጠበቅ አመልክተዋል።


ኢትዮጵያ የምታካሂደዉ ታላቁ ህዳሴ በመባል የሚታወቀዉ የግድብ ግንባታ በግብፅና ሱዳን ላይ የሚያመጣውን ተፅዕኖ ለማጥናት ሦስቱ አገሮች ያቋቋሙት የጋራ ኮሚቴ፣ ሁለት ዓለም አቀፍ ኩባንያዎችን ያካተተ ነዉ። ለዚህም በምሕፃሩ BRL በመባል የሚታወቀዉ የፈረንሣይ ኩባንያ እና ከኔዘርላንድ ዴልታሬስ ኩባንያ መመረጣቸዉን ዘገባዎች ይተቁማሉ፡፡ ይሁን እንጂ ዴልታረስ የተሰኘዉ ኩባኒያ፣ የፕሮጀክቱን ጥናት 30 በመቶ እንዲይዝ ቢታቀድም፣ ኩባንያዉ ራሱን ከጥናት ሥራው ማግለሉን በመስከረም ወር አጋማሽ ላይ በድረገጹ አሳውቋል፡፡ እንደ ኢንጅነር ተሾመ ገለጻ ሊካሄድ የታቀደዉ ስብሰባ ዋና ዓላማም በሁለቱ ኩባኒያዎች መሃል የተፈጠረዉን ልዩነት ለመመልከት እና በቀጣይም ሥራዉ እንዴት መሆን እንዳለብት ለመወያየት ነዉ።

Nil Dammbau in Äthiopien Archiv 28.05.2013
ምስል William Lloyd-George/AFP/Getty Images


የኔዜርላንዱ ኩባንያ በድረገጹ ላይ ራሱን ከጥናቱ ማግለሉን ቢያሳዉቅም ለኢትዮጵያ ግን በጹሑፍ መቶ በመቶ መዉጣቱን እንዳልገለጸ በማመልከትም ሁለቱ ኩባንያዎች አብረዊ የሚሠሩበት አለያም ሥራዉ የምሠራበትን ሁኔታ እንደሚመቻች ኢንጅነር ተሾመ ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል።


ድርድር ሁሌም ወጣገቦች እንዳሉት የገለፁት በኢትዮጵያ የሰላም እና ልማት ዓለም አቀፍ ተቋም ከፍተኛ ተመራማር የሆኑት አቶ አበበ አይንቴ፣ አለመስማማቱ መሠረታዊ ልዩነት ካላመጣ ወይም እስካልፈጠረ ድረስ ሙሉ በሙሉ ማስቀረት እንደማይቻል አክለዉ አብራርተዋል። ይህ የሶስትዬሽ ድርድር ወደዬት ሊያመራ ይችላል ለሚለዉ አቶ አበበ ሲያስረዱ፣
ድርድሩ እንደሚቀጥል እምነት እንደላቸዉ በመጥቀስ፤ ክፍተት የተፈጠረዉ በአገሮቹ ሳይሆን በአማካርዮቹ ሰበብ ስለሆነ ያም ተነጋግሮ እና ተስማምቶ ስለተፈታ ሂደቱ በተያዘለት መርሃግብር እና በተያዘዉ የመወያያ ነጥብ ላይ እንደሚቀጥል አቶ አበበ አብራርተዋል።


የጋራ የቴክኒክ ኮሚቴዉ ስድስት አባላት የያዘ ሲሆን፣ በግድብ ሥራ፣ በዉኃ ምንጭና በአከባብ ጥበቃ ላይ አራት የዓለም አቀፍ ባለሙያዎችንም እንዳካተተ ዘገባዎች ያሳያሉ።

መርጋ ዮናስ

ሸዋዬ ለገሠ