1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የቦኮሃራም እገታ እና መዘዙ

ሐሙስ፣ ሚያዝያ 10 2011

በእገታው ሰበብ ወላጆች አሁንም ልጆቻቸውን ወደ ትምሕርት ቤት ለመላክ ይፈራሉ። በዚህ የተነሳም ትምሕርት ቤት የሚሄዱ ህጻናት ቁጥር ቀንሷል።እናም  የምዕራባውያን ትምሕርት ሀራም ነው የሚለው ቦኮሀራም ዓላማውን ያሳካ ይመስላል።የተመ የህጻናት መርጃ ድርጅት ዩኒሴፍ በሰሜን ምሥራቅ ናይጀሪያ ካሉ ህጻናት 53 በመቶው ብቻ ናቸው ትምህርት ቤት የሚሄዱት።

https://p.dw.com/p/3H2kP
Boko Haram lässt entführte Mädchen frei
ምስል Reuters/O. Lanre

የቦኮሃራም እገታ መዘዝ

ቺቦክ ከተባለው ሰሜን ምሥራቅ ናይጀሪያ ውስጥ ከሚገኘው የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት 276 ተማሪዎች ከትምህርት ገበታቸው ላይ ታፍነው ከተወሰዱ 5 ዓመት አለፈ።ያኔ የታገቱት ተማሪዎች የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂያ ፈተና ለመውሰድ ጥቂት ጊዜያት ብቻ የቀራቸው እድሜያቸው ከ16 እስከ 18 ዓመት የሚሆን ልጃገረዶች ነበሩ።ቦኮሀራም የተባለው በናይጀሪያ እና በጎረቤት አገራት ተደጋጋሚ ጥቃት የሚጥለው ቡድን ካገታቸው ከነዚሁ ተማሪዎች ውስጥ አብዛኛዎቹ ቢመለሱም አሁንም ቡድኑ ያልለቀቃቸው ተማሪዎች አሉ። ይህ እገታ ባስከተለው ፍርሃት ምክንያት በአሁኑ ጊዜ ሰሜን ናይጀሪያ ውስጥ ወደ ትምህርት ቤት የሚላኩ ልጆች ቁጥር በአሳሳቢ ሁኔታ ቀንሷል።የዶቼቬለው ላጠናቀረው ዘገባ ኂሩት መለሰ።
ቦኮሃራም ከአምስት ዓመት በፊት ከሰሜን ናይጀሪያ ካገታቸው የቺቦክ ልጃገረዶች አብዛኛዎቹ ተለቀው በመንግሥት መርሃ ግብር ድግፍ እየተደረገላቸው ነው። ሆኖም አሁንም ቦኮሀራም ያልለቀቃቸው የ112 ልጆች እጣ ፈንታ ግልጽ አይደለም። ሁሉም በህይወት መገኘታቸው ያጠራጥራል። ከዚህ ሌላ በእገታው ምክንያት ወላጆች አሁንም ልጆቻቸውን ወደ ትምሕርት ቤት ለመላክ ይፈራሉ። በዚህ የተነሳም በአካባቢው ትምሕርት ቤት የሚሄዱ ህጻናት ቁጥር ቀንሷል።እናም  የምዕራባውያን ትምሕርት ሀራም ነው የሚለው ቦኮሀራም ዓላማውን ያሳካ ይመስላል። የተመ የህጻናት መርጃ ድርጅት ዩኒሴፍ እንደሚለው በሰሜን ምሥራቅ ናይጀሪያ ከሚገኙ ህጻናት 53 በመቶው ብቻ ናቸው ትምህርት ቤት የሚሄዱት። ቦኮሃራም በሌሎች አካባቢዎች ከ1ሺህ በላይ ህጻናትን አግቷል፤ከ2ሺህ በላይ መምህራንን ገድሏል ወደ 20 ሺህ ሰዎችን ደግሞ አፈናቅሏል። የ1400 ትምህርት ቤቶች ወድመዋል፤ አብዛኛዎቹም እስካሁን እንደተዘጉ ነው። አልሀይ በሽር መሐመድ የ9 ልጆች አባት ነው። ከእገታው በኅላ ልጆቹን ወደ ትምህርት ቤት ለመላክ ፈቃደኛ አይደለም። 
«እውነት ለመናገር ልጆቻችን ወደ መንግሥት ትምህርት ቤቶች ልንወስድ አንችልም። ምክንያቱም በቂ የፀጥታ ጥበቃ የለም።ልጆቻችንን ትምህርት ቤት ብንልካቸው እንኳን መንግሥት እነርሱን ለመጠበቅ ምንም ዓይነት እርምጃ አይወስድም።ስለዚህ ልጆቻችንን ወደ ትምሕርት ቤት መልሰን ለመላክ አይቻለንም።»
እንዲህ ዓይነቱ ችግር የተከሰተው በናይጀሪያ ብቻ አይደለም። በናይጀሪያ ጎረቤት በካሜሩንም ጭምር እንጂ። ቦኮሃራም በካሜሩን ትምሕርት ቤቶችን ያቃጥላል፤ህጻናት እና ወጣቶችን ይጠልፋል፤በአጥፍቶ ጠፊነት እንዲሰማሩም ይመለምላል። አብዱራህማን ቤሎ የ17 ዓመት ወጣት ነው። የቦኮሃራም ተዋጊዎች ናይጀሪያ ድንበር አቅራቢያ ካሜሩን ውስጥ ፎቶኮል በተባለው ቦታ  ከሚገኘው ትምህርት ቤት አግተውት ወደ ዛምቢዛ ጫካ ይወስዱታል። ለነርሱ ሲላላክ እና ሲሰልል ቆይቶ በመጨረሻ ነጻ ሊወጣ ችሏል ።ከዚያ በኋላ ወደ ሚጠለፍበት ትምሕርት ቤት ላለመመለስ ወሰኖ ነበር። ትምሕርት ቤት የማይሄዱት ተማሪዎች ብቻ አይደሉም መምህራንንም ጭምር እንጂ በካሜሩን 600 የሚሆኑ ለህይወታቸው የሚሰጉ መምህራን ለማስተማር ፈቃደኛ አይደሉም። ከመካከላቸው አንዷ ፓትሪስያ ንጉም አንዷ ናት። 
« ልገደል የምችልበት ቦታ እንድሄድ ትጠብቃለህ?እኔ ላስተምራቸው የሚገባ ተማሪዎች በሌሉበት ትምሕርት ቤት ትሄዳለች ብለህ ትጠብቃለህ?ትምሕርት ቤቶች ይቃጠላለሉ፤ሰዎች ይጠለፋሉ።ሰዎች ራሳቸውን አጥፍተው ሌሎችንም የሚገድሉባቸው አጥፍቶ ጠፊዎች ቦብም ያፈነዳሉ፤እናም በዚህ አካባቢ ለስራ ስትመደብ ምን ሊደርስብህ እንደሚችል እርግጠኛ አይደለህም ።»
በሰሜን ካሜሩን  የትምሕርት ጉዳዮች ተጠሪ ሳንዳ ኁዋ ትምህርት ቤት የሚሄዱ ህጻናት ቁጥር አነስተኛ መሆኑን አረጋግጠዋል። 
«ያለፈው የትምሕርት ዓመት ሲያበቃ 124 ትምሕርት ቤቶች ተዘግተው ነበር። በመጨረሻ የደረሰው የአጥፍቶ ጠፊ ጥቃት ትምሕርት ቤቶች በትክክል እንዳይሰሩ ገድቧል።በዚህ ዓመት በጥር ወር ብቻ 3 ትምሕርት ቤቶችን ለመዝጋት ተገደናል።» 
ካሜሩን የሚገኘው አብዱራህማን ቤሎ ምንም እንኳን ሁኔታው አደናባሪ ቢሆንም ፣ አሁን ወደ ትምሕርት ቤት መመለስ እንዳለበት ራሱን አሳምኖ መማር ጀምሯል።የካሜሩን የትምህርት ሚኒስቴር ደግሞ ወላጆች ልጆቻቸውን ወደ ትምሕርት ቤት እንዲልኩ ለማሳመን እየሞከረ ነው። 

Nigeria Armee rettet Mädchen
ምስል picture-alliance/dpa/EPA/Nigerian Army
Nigeria Dapchi Schülerinnen nach Boko-Haram-Angriff auf Schule vermisst
ምስል Reuters/O. Lanre
Nigeria - Heimkehr der Chibok Mädchen
ምስል picture-alliance/dpa/AP/O. Gbemiga

ኂሩት መለሰ

ማንተጋፍቶት ስለሺ