“ህገወጥ እንቅስቃሴ የሚያደርጉ ኃይሎችን እያባበልን አንቀጥልም”- የአዴፓ ጽህፈት ቤት ኃላፊ
ሰኞ፣ ግንቦት 26 2011የአማራ ክልል ገዢ ፓርቲ አዴፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት በክልሉ ባሉ ችግሮች ላይ ከወረዳ ጀምሮ በተለያየ ደረጃ የድርጅቱ አመራሮች ጋር ሲያደርግ የቆየውን ውይይት አገባድዷል። በውይይቱ ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የአዴፓ ሊቀመንበር አቶ ደመቀ መኮንን ተገኝተዋል።
የፓርቲው የጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዩሃንስ ቧያለው በውይይቱ ላይ ስለተነሱ ጭብጦች ዛሬ መግለጫ ሰጥተዋል። አቶ ዩሃንስ የአመራር አመዳደብና አጠቃላይ የድርጅቱን አወቃቀር በተመለከተ ውይይት መደረጉን አመልክተዋል።
የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በክልሉ ሰላም እንዲሰፍን የሚጠይቁ ሰላማዊ ሰልፎች እያካሂዱ መሆኑን ያነሱ ጋዜጠኞች የህዝቡን ጥያቄ እንዴት ፓርቲው እንዴት እንደሚመለከተው ጠይቀዋል። "የህገመንግስት ይሻሻልልን" ፣ "የወሰን ጥያቄ ምላሽ አላገኘም" እና ሌሎችም ጥያቄዎች በህብረተሰቡ እንደሚነሱ ጋዜጠኞቹ ጠቅሰዋል። "አዴፓ በክልሉ ሰላም ለምን ማስፈን ተሳነው?" የሚል ጥያቄም ቀርቦ ነበር።
በጋዜጠኞች ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት የፓርቲው የጽህፈት ቤት “ህግ እና ስርዓትን የሚጥሱ እና ህገወጥ እንቅስቃሴ የሚያደርጉ ኃይሎች እያባበልን አንቀጥልም” ብለዋል። የጸጥታ ኃይሎች የማያዳግም እርምጃ መውሰድ እንደሚጀምሩም ገልጸዋል።
በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስ መምህር አቶ ቻላቸው ታረቀኝ "አዴፓ እውነተኛ ለውጥ እንዲመጣ ከሻተ የመግለጫ ጋጋታ ሳይሆን ብቃት ያለውን አመራር መመደብ ነው መፍትሔው" ሲሉ ለዶይቼ ቬለ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
ከወራት በፊት የአገሪቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን እና ሌሎች ከፍተኛ ሹማምንት በተገኙበት በዋናነት በክልሉ በፀጥታ ላይ ያተኮረ ውይይት ውይይት በባህር ዳር መካሄዱ ይታወሳል። በውይይቱ ላይ የፌደራል የደህንነት ኃላፊዎች፣ የጦር ኃይሎች ኢታማዦር ሹም፣ የፖሊስ እና ሌሎችም ከፍተኛ የፌደራል እና የክልል አመራሮች ተሳትፈው ነበር።
ዓለምነው መኮንን
ተስፋለም ወልደየስ
ማንተጋፍቶት ስለሺ