1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ፈረንሳይ ላይ በደረሰዉ ጥቃት ቢያንስ 84 ሰዎች ተገደሉ

ዓርብ፣ ሐምሌ 8 2008

የባሕር ዳርቻዋ የፈረንሳይ ኒስ ከተማ ላይ በተቃጣ የሽብር ጥቃት ቢያንስ 84ሰዎች ተገደሉ። አንድ ከባድ የጭነት ማመላለሻን የያዘ ግለሰብ ሕዝብ በተሰበሰበት ቦታ ላይ በፈጣን በማሽከርከር ነዉ ይህን ያህል ሕዝብ ለመጥፋት የበቃዉ። ግለሰቡ በፖሊሶች ተገድሎአል።

https://p.dw.com/p/1JPDK
Frankreich Anschlag Lastwagen-Attacke in Nizza
ምስል picture-alliance/dpa/O. Anrigo

የዚህ ጥቃት መንስኤና ምንነት ግን እስካሁን በዝርዝር አይታወቅም። የፈረንሳይ ሕዝብ ብሔራዊ ቀን በሚከበር በትናንትናዉ ዕለት ምሽት ላይ በዓሉን በማክበርና የርችት ተኩስ ለማየት ተሰብስቦ በነበረበት ሕዝብ ላይ ነዉ ጥቃቱ አድራሹ ግለሰብ የያዘዉን ከባድ የጭነት መኪና በከባድ ፍጥነት ሕዝብ በተሰበሰበት መካከል ያሽከረከረዉ ። በዚህ ጥቃት ሕጻናትም ተገድለዋል። በጥቃቱ 18 ሰዎች ለሕይወት በሚያሰጋ ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ የፈረንሳይ የሃገር ዉስጥ አስተዳደር ሚንስትር ቤርናድ ካዛነቭ ገልፀዋል። የፈረንሳይ ብዙኃን መገናኛዎች በጥቃቱ ከ 100 በላይ ሰዎች ጉዳይት እንደደረሰባቸዉ እየዘገቡ ነዉ። ከባድ ተሽከርካሪዉን በሰዎች መካከል በማሽከርከር ቢያንስ 84 ሰዎችን የገደለዉ ግለሰብ እስኪገደል ድረስ በከፍተኛ ፍጥነት ሁለት ኪሎሜትር ያህል መጓዙ ተዘግቦአል። ፖሊስ ባወጣዉ መግለጫ ይህን አደጋ በተፈፀመበት ተሽከርካሪ ዉስጥ የ 31 ዓመት ትዉልደ ቱኒዝያዊ የፈረንሳይ ዜጋ መታወቅያ ተገኝቶአል። በዚሁ ተሽከርካሪ ዉስጥ መሳርያና ቦንቦች መገኘቱን የአካባቢዉ ፕሬዚዳንት ክርስትያን ኢስትሮሲ ተናግረዋል። በፈረንሳይ የደረሰዉን ጥቃት ተከትሎ የነበረዉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለሦስት ወራት ተራዝሞአል። በፈረንሳይ የዛሬ ስምንት ወር ግድም አሸባሪዎች ጥቃት አድርሰዉ ከመቆ በላይ ሠዎች መገደላቸዉ ይታወሳል። የዓለም ሃገር መንግሥታት በፈረንሳይ የተፈፀመዉን ጥቃት በማዉገዝ ለሃገሪቱ የሃዘን መግለጫን በማስተላለፍ ላይ ይገኛሉ።

አዜብ ታደሰ