ጉልበት ሰጭ መድኃኒትና የኢትዮጵያ አትሌቲክስ
ማክሰኞ፣ የካቲት 22 2008የኢትዮጵያ የፀረ ጉልበት ሰጪ መድኃኒት መሥሪያ ቤት ዋና ጸሐፊ አቶ ሰሎሞን መዓዛ እንዳስታወቁት፣ ጉልበት ሰጪ መድሀኒት ተጠቅማችኋል በመባል የተጠረጠሩት አትሌቶችን ምርመራ የሚያካሂደው የዓለም አትሌትክስ ፌዴሬሸን ማህበር ነው። አቶ ሰለሞን ግን የአትሌቶቹ ማንነትም ሆነ ወሰዱት የተባለው የመድሀኒት ዓይነት ምንነትን ከመናገር ተቆጥበዋል። ምርመራውን እያካሄደ ያለዉ የዓለም አትሌትክስ ፌዴሬሸን ማህበር ከኢትዮጵያ የአትሌትክስ ፌዴሬሽን ጋር በመተባበር በመሥራት ላይ ይገኛል።
የአዲስ አበባ የስፖርት ጋዝጤኛዉ ምስጋናዉ ለዶይቸ ቬሌ እንደተናገረው፣ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሸን ዛሬ ጥዋት ይፋዊ ያልሆነ ስብሰባ አካሂዶ ታዋቂ አትሌቶች ይህን ጉዳይ አስመልክተው ለሌሎች ልምዳቸዉን እንዲያካፍሉ ጠይቆዋል። ጉዳዩ በአብዛኛዉ ህዝብ ዘንድ ድንጋጤ መፍጠሩን ምስጋናዉ ገልጾዋል።
የምርመራው ውጤት እስኪታወቅ ድረስ ህብረተሰቡ መደምደሚያ ሀሳብ ላይ ከመድረስ እንዲቆጠብ ያሳሰበው ታዋቂዉ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ጉዳዩ አሉታዊ የሆነ ተፅዕኖ ሊኖረው እንደሚችል ለዶይቼ ቬለ ተናግሮዋል።
በዙህ ጉዳይ ላይ በዶቼ ቬለ የፌስቡክ ድረ ገፅ ላይ የተወያዩ ተሳታፊዎች ይህ ቅሌት እዉን ከሆነ ትልቅ ተፅዕኖ እንደሚያሳድር እና ተጠያቂ የሚደረገውም የአትሌቲክሰ ፌዴሬሸኑን መሆኑን አስታውቀዋል።
መርጋ ዮናስ
አርያም አብራሃ