1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዶክተሮች ለኢትዮጵያ

ረቡዕ፣ ኅዳር 28 2009

ጀርመን ዉስጥ ከተመሠረተ ብዙም ጊዜ ያልሆነዉ አንድ ማኅበር በኢትዮጵያ አንድ ሃኪም ቤት የተሻለ የህክምና አገልግሎት ለመስጠት እንዲችል እገዛዎችን ለማድረግ መንቀሳቀስ ጀምሯል። ጀርመናዉያን የህክምና ባለሙያዎችን ያካተተዉ የዚህ ማኅበር እንቅስቃሴም በሀገሪቱ የሕፃናት እና እናቶችን ሞት ለመቀነስ የበኩሉን አስተዋፅኦ የማድረግ ዓላማ ሰንቋል።

https://p.dw.com/p/2Tq8R
Ärzte für Äthiopien e.v. Lieferung Yiragalem Krankenhaus
ምስል Ärzte für Äthiopien e.v.

ዶክተሮች ለኢትዮጵያ

ዶክተሮች ለኢትዮጵያ፤ በጀርመንኛዉ አርትስት ፉዩር ኤትዮፕየን የተሠኘዉ ማኅበር መሥራች እና የሃሳቡም ጠንሳች ናቸዉ ወይዘሮ ትዕግሥት ላቀዉ መብራቱ። የቆመን ሳይሆን መንቀሳቀስ የጀመረን መግፋት ፈጥኖ እንዲሄድ ያደርጋል የሚሉት ወ/ሮ ትዕግሥት እህታቸዉን ጨምረዉ በብዙዎች ዘወትር ስለችግሯ በሚነገርላት መገኛቸዉ በሆነችዉ ኢትዮጵያ የበኩላቸዉን ለማድረግ እየሞከሩ ነዉ።

ወደጀርመን ሃገር ዲፕሎማት በነበሩት አባታቸዉ ሥራ ምክንያት ነዉ የዛሬ 40 ዓመት ገደማ የመጡት፤ ወ/ሮ ትዕግሥት ላቀዉ። ቤተሰቦቻቸዉ በዚህ ሀገር ሲያሳድጓቸዉም የኢትዮጵያንም ሆነ የጀርመንን ባህል አክብረዉ እና እሳቸዉ እንደሚሉትም ጥሩ ጥሩዉን ወስደዉ አሁን ለደረሱበት እንደበቁ ይናገራሉ ወ/ሮ ትዕግሥት። ይህ ደግሞ የሀገር ፍቅርን በዉስጣቸዉ እንዳሳደገም ያምናሉ። በዚህ ምክንያትም በሥራ ጉዳይ ከሚቀርቧቸዉ ጀርመናዉያን ጋር ስለሀገራቸዉ በሚያደርጉት ዉይይት አንዳች ነገር የመሥራት ሃሳብ ተጠነሰሰ። ማኅበሩ ከተመሠረተ አንድ ዓመት ከመንፈቅ ቢሆነዉም በዚህ ጊዜ ዉስጥ ትርጉም ያላቸዉ እንቅስቃሴዎችን ማድረጉን ለመረዳት ችለናል። ማኅበሩ በህክምና ዘርፍ የተሰማሩ ባለሙያዎች ስብስብ እንደመሆኑ ምን እንሥራ ብለዉ ሲወያዩ ከሀኪም ቤት ጋር መሥራት ላይ ይስማሙ እና አብረዉት የሚሠሩት ሃኪም ቤትን የሚያገኙበትን መንገድ አፈላለጉ። ዶክተሮች ለኢትዮጵያ ማኅበር ይርጋለም ጠቅላላ ሆስፒታልን ለመደገፍ እንዴት መረጠዉ? ወ/ሮ ትዕግሥት ያስረዳሉ፤

Ärzte für Äthiopien e.v. Lieferung Yiragalem Krankenhaus
ወ/ሮ ትዕግሥት ላቀዉምስል Ärzte für Äthiopien e.v.

በይርጋለም ጠቅላላ ሃኪም ቤት በወቅቱ ለሕፃናት እና እናቶች ተገቢዉን ህክምና ለመስጠት እንዲያስችል በሚል የተጀመረዉ ከጀርመን በህክምናዉ ዘርፍ ለመርዳት ያቀደዉን የዶክተሮች ለኢትዮጵያ ማኅበር ቀልብ በዚህ መልኩ ሳበ። እዚህ ሀገር የተማርኩት ይላሉ ወ/ሮ ትዕግሥት፤ የቆመን በመግፋት ኃይል መጨረስ ሳይሆን የሚንቀሳቀስን መደገፍ ነዉ።

ማኅበሩ ያቀደዉን ዓላማ ተግባራዊ ለማድረግ በጀመረዉ እንቅስቃሴም በአጭር ጊዜ ዉስጥ ሀኪም ቤቱ ዉስጥ እጅግ ያስፈልግ የነበረዉን የማጠቢያ ማሽን፣  ጨምሮ ሌሎች ቁሳቁሶችንም ለሀኪም ቤቱ ማቅረብ መቻሉን የማኅበሩ የቦርድ አባል ዶክተር ሚሻኤል ኤልበርፌልድ ይናገራሉ።

«ለመጀመሪያ ጊዜ ከፍተኛ የህክምና እርዳታችንን እዚያዉ አድርሰናል። ይኸዉም የተለያዩ የህክምና እቃዎች ማለት መንቀሳቀሻ ተሽከርካሪ ወንበሮች፤ የሀኪም ቤት አልጋዎች፣ ፍራሾች፤ እንዲሁም ተገቢዉን የሀኪም ቤት ንፅህና መጠበቅ የሚያስችል ግዙፍ ልብስ ማጠቢያ ማሽን፤ አልትራ ሳዉንድ ማሽን፣ እና ለሚገነባዉ የሕፃናት እና እናቶች ሃኪም ቤት ሊደግፉ የሚችሉ ነገሮችን ወስደናል።»

የዉስጥ እና አጠቃላይ ህክምና ባለሙያዉ ዶክተር ኤልበርፌልድ ወደ ኢትዮጵያ ባለፈዉ ዓመት ከተጓዙት የማኅበሩ አባላት አንዱ ናቸዉ። የጀርመን እና የኢትዮጵያን የህክምና ሁኔታ ማነፃፀር ባይቻልም በበኩላቸዉ ሊያደርጉት ያቀዱትን እንዲህ ገልፀዉታል።

Ärzte für Äthiopien e.v. Lieferung Yiragalem Krankenhaus
ማጠቢያዉ ማሽንምስል Ärzte für Äthiopien e.v.

«እንዳልሽዉ የሁለቱን የህክምና አገልግሎት ስርዓት ማወዳደር አይቻልም፤ የበሽታዉን ገፅታም እንዲሁ ማነፃፀር አይቻልም፤ በጀርመን እና ኢትዮጵያ የህክምናዉ አቅርቦትም ቢሆን ልዩነቱ ግልፅ ነዉ። ይህም ቢሆን ግን እዚያ የሚገኙት ዶክተሮች ባሉት መጠነኛ የህክምና ቁሳቁሶች በሽተኞቻቸዉን ማከም ይችላሉ የሚል ተስፋ አለን።»

በተቻለ መጠን ተገቢዉን ህክምና ለበሽተኞቹ የማቅረቡ ጥረት እንዳለ ሆኖም ከምንም በላይ የህክምና መስጫዉ አካባቢ የፀዳ እንዲሆን ማድረጉም ዋና ግባቸዉ መሆኑም ይናገራሉ ዶክተር ኤልበርፌልድ፤

«ግባችን ከኢትዮጵያ ዶክተሮች ጋር በምናደርገዉ የጋራ ትብብር ሥራ የንፅህናዉ ደረጃ እንዲሻሻል በማድረግ፤ እዚያ ለሚገኙት የህክምና አገልግሎት ፈላጊዎች አቅርቦቱ እንዲሻሻል፤ በዚህም የሕፃናት ሞት ወይም በወሊድ ጊዜ ሕይወታቸዉ የሚያልፍ እናቶች ቁጥር እንዲቀንስ ማድረግ ነዉ የእኛ ግብ።»

የበኩልን አስተዋፅኦ ለማድረግ መንቀሳቀስ አንድ ነገር ቢሆንም ብዙዉን ጊዜ እንዲህ ያሉ አገልግሎቶችን ማድረግ የሚፈልጉ ወገኖች በሚገጥማቸዉ የቢሮክራሲ ዉጣ ዉረዶች ምክንያት ሲማረሩ መስማት የተለመደ በመሆኑ፤ ለመሆኑ እናንተ እንዲህ ካለዉ ሃሳባችሁ ጋር ወደ ይርጋለም ጠቅላላ ሃኪም ቤት ስትሄዱ ትብብሩም ሆነ ዝግጁነቱ እንዴት ነበር አልኳቸዉ ዶክተር ሚሻኤል ኤልበርፌልድን።

«በጣም አስደናቂ ነበር። ዝግጁነቱ በጣም በጣም ከፍተኛ ነበር። የሙያ ባልደረቦቻችን ግልፅነት በጣም ከፍተኛ ነበር። ከመጀመሪያዉ እኛ ይህን አድርጉ ያን አታድርጉ ልንል አልመጣንም ብለናቸዉ ነበር ከመጀመሪያዉ፤ እኛ የሄድነዉ የበለጠ በማወቅ የበኩላችንን ልንረዳቸዉ መሆኑን ነግረናቸዋል። በጋራ በምናከናዉነዉ ተግባርም ምናልባት የሆነ ነገር ማመቻቸት እንድንችል ነዉ። ምናልባት ከሥራ ልምዳችን በማጋራት ልንረዳ መሞከር ነዉ ያልናቸዉ እናም የዶክተሮቹ ዝግጁነት እና ግልፅነት እጅግ ከፍተኛ እና ግሩም ነበር።»

Ärzte für Äthiopien e.v. Lieferung Yiragalem Krankenhaus
ለይርጋለም ጠቅላላ ሆስፒታል የሚላኩ ዕቃዎች ምስል Ärzte für Äthiopien e.v.

እናም ይላሉ ዶክተር ሚሻኤል ኤልበርፌልድ ከፊታችን ብዙ ሥራ ይጠብቀናል፤ ያም ቢሆን ግን ይህ የተጀመረዉ እያደገ ሄዶ ሀኪም ቤቱ እንዳሰብነዉ የተሻለ የህክምና አገልግሎት ሲሰጥ ለማየት እንጥራለን። በመድኃኒት አቅርቦት ሥራ የተሰማሩት ወ/ሮ ትዕግሥት እንደ ዶክተር ኤልበርፌልድ ያሉትን የዓላማቸዉ ተባባሪ የሆኑትን ጀርመናዉያን ስለ ሀገራቸዉ ባህል በማስተዋወቅ ብቻ ሳይወሰኑ ለዚህ ተግባር ሲያንቀሳቅሱ አንድ ዓላማ በዉስጣቸዉ ይዘዉ ነበር።

ዶክተር ድንቅዬ አበበ የይርጋለም አጠቃላይ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር እና የዉስጥ ደዌ ህክምና ባለሙያ ናቸዉ። ከዓመት በፊት ዶክተሮች ለኢትዮጵያ ማኅበር ከእነሱ ሃኪም ቤት ጋር አብሮ ለመሥራት ከወሰነ በኋላ የነበረዉን ያስታዉሳሉ። ወደ,15 ሚሊየን የሚጠጋ ብር በየሲዳማ ዞን አስተዳደር ሙሉ በሙሉ ወጪዉን ሸፍኖ የተገነባዉ የእናቶች እና ሕፃናት ሃኪም ቤት ሕንፃ ሥራ መጠናቀቁን ያመለከቱት ዶክተር ድንቅዬ፤ ሕንጻዉ ቢሠራም አገልግሎት እንዳልጀመረ ገልጸዉልናል። ምክንያቱንም ያስረዳሉ። ሙሉ ቅንብሩን ከድምፅ ዘገባዉ ያድምጡ!

ሸዋዬ  ለገሠ

አርያም ተክሌ