ዶናልድ ትራምፕ አሸነፉ
ረቡዕ፣ ጥቅምት 30 2009
45ኛ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የሚሆኑት ትራምፕ በምርጫዉ 289 ድምፅን በማግኘት ያሸነፉ ሲሆን፤ የቀድሞዋ ቀዳማዊት እመቤት፤ ሴናተር እና ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሒላሪ ክሊንተን 215 ድምፅ ማግኘታቸዉ ታዉቋል። ዶናልድ ትራምፕ ከምርጫ ዉጤት በኋላ ባደረጉት ንግግር ለሁሉ አሜሪካዉያን ፕሬዚዳንት መሆን እፈልጋለሁ ሲሉ ተደምጠዋል። ሚንስትር ሒላሪ ክሊንተን የምርጫዉ ዉጤት ይፋ ከሆነ በኋላ ወጥተዉ ለደጋፊዎቻቸዉ ንግግር አለማድረጋቸዉ ለብዙዎች ጥያቄን አጭሮአል። የአሜሪካን ምርጫና ዉጤቱን ተከትሎ የጀርመን ፖለቲከኞች ዉጤቱን አስደንጋጭ ሲሉ ነዉ የገለጹት። አንዳንድ የመረጃ መዘርዝሮች እንደሚያሳዩት ዶናልድ ትራምፕን የመረጡት ወጣቶች ሳይሆኑ በእድሜ በሰል ያሉ አሜሪካዉያን ናቸዉ፤ ወጣቶች በአብዛኛዉ ድምፅ የሰጡት ለሒላሪ ክሊንተን ነዉ። ምርጫው አማሪካዉያንን ለሁለት ሳይከፍል አልቀረም ሲሉ የፖለቲካ ተንታኞች ሃሳብ ሲሰነዝሩ ተሰምተዉ ነበር። አሜሪካዉን ትናንት የወደፊት ፕሬዝደንታቸዉን ለመምረጥ እንደየአሉበት አካባቢ የሰዓት አቆጣጠር ድምፅ ሲሰጡ ነበር ያረፈዱት። አሰልቺ፤ አንዱ ሌላዉን በማጥላላትና መተች ላይ የተመሠረተዉ የምርጫ ዘመቻ የሐገሪቱን ሕዝብ እሁለት የተራራቀ ጎራ እንደገመሰዉም ተዘግቦ ነበር። ታዛቢዎች እንዳሉት መራጩ ሕዝብ የዲሞክራቲክ ፓርቲዋን እጩ ሒላሪ ክሊንተንን ወይም የሪፐብሊካን ተቀናቃኛቸዉን ዶናልድ ትራምፕ ለመምረጥ ደምፁን የሚሰጠዉም በተከፋፈለ ስሜትና ልብ ነዉ። የቀድሞዋ ቀዳማዊት እመቤት፤ ሴናተር እና ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሒላሪ ክሊንተን ከባለቤታቸዉ ከቀድሞዉ ፕሬዝደንት ቢል ክሊንተን ጋር ሆነዉ በሚኖሩበት ቀበሌ ቻፓኩዋ-ኒዮርክ ላይ ትናንት ጧት ድምፃቸዉን ሰጥተዉ ነበር። ክሊንተን ድምፃቸዉን ሲሰጡ ፤ ከተመረጡ «አብሮ የሚመጣ» ያሉትን ከባድ ሐላፊነት ለመወጣት እንደሚጥሩ ቃል ገብተዉ ነበር። ተቀናቃኛቸዉ ዶናልድ ትራምፕ ስቱዲዮ እስከገባንበት ጊዜ ድረስ ድምፅ ባይሰጡም በትዊተር ባሰራጩት መልዕክት «ዛሬ እናሸንፋለን» ብለዉ ነበር። «ዋይት ሐዉስን ዳግም እንቆጣጠራለንም።» የሕዝብ አስተያየት መመዘኛዎች እንደሚያመለክቱት ክሊንተን ከትራምፕ ከ3.3 እስከ 6 በመቶ የሚደርስ ብልጫን አሳይቶ ነበር። ዬኤስ አሜሪካ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ አሸናፊ የሪፓብሊካኑ ዶናልድ ትራምፕ ወደ ዋይት ሃዉስ የሚያስገባቸዉን መንገድ ጠርገዉ፤ ቁልፉን ለመቀበላቸዉ ማረጋገጫን አግኝተዋል። የአሜሪካን ምርጫ ሂደት እና የምርጡኝ ዘመቻው በኢትዮጵያውያን አሜሪካውያን እንዴት ነበር የገሙት? የዋሽንግተኑ ወኪላችን ዘገባ ልኮልናል።
መክብብ ሸዋ
ነጋሽ መሐመድ
አዜብ ታደሰ