ዶ/ር ወልደ መስቀል ኮስትሬ አረፉ
ሰኞ፣ ግንቦት 8 2008ዶ/ር ወልደ መስቀል በጎርጎሮሳዊዉ 1972 በጀርመን የሙኒክ ኦሎምፒክ ላይ የተሳተፈዉ የኢትዮጵያ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ለነበሩት ንጉሤ ሮባ ምክትል አሰልጣኝ በመሆን ነበር፤ ወደ አሰልጣኝነቱ ዓለም የገቡት። ወልደ መስቀል ኮስትሬ በጎርጎሮሳዊዉ 1982 ዓ,ም በሀንጋሪ የሁለተኛ ዲግሪያቸዉን ከተቀበሉ በኋላ ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰው በስፖርት ኮሚሽን በከፍተኛ ባለሞያነትም ሠርተዋል። ዶክተር ወልደ መስቀል ኮስትሬ በጎርጎሮሳዊዉ 1992 ዓ,ም ከተካሄደዉ ከባርሴሎና ኦሎምፒክ በዚሁ ዘመን 2008 ዓ,ም ላይ ስለከተካሄደዉ የቤጂንጉ ኦሎምፒክ ድረስ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ሆነዉ ሲያገለግሉ ኢትዮጵያ በዓለም አደባባይ ስሟ ከፍ ብሎ እንዲጠራ ያደረጉትን የ5,000 እና የ10,000 ሜትር ባለድል አትሌቶች አፍርተዋል። ዶ/ር ወልደ መስቀል የብሔራዊ ቡድኑ አሰልጣኝ ሆነዉ በተሳተፉባቸዉ አምስት የኦሎምፒክ ዉድድሮች ለኢትዮጵያ 13 የወርቅ 5 የብር እና 10 የነሐስ በድምሩ 28 ሜዳሊያዎችን ማስገኘታቸዉ ተመዝግቦላቸዋል። የዛሬ 10 ዓመት ዓለም አቀፍ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በአትሌቲክሱ ዓለም ለአሰልጣኞች የሚሸለመውን የዓመቱ ምርጥ የአሰልጣኝነት ሽልማት አበርክቶላቸዋልም።ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን ኢትዮጵያዉያን ሯጮችን ለድል ያበቁ የአትሌቲክስ አሰልጣኝ ዶክተር ወልደ መስቀል ኮስትሬ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸዉን መስማቱ እንዳሳዘነዉ በድረ-ገፁ ላይ አስነብቦአል።
ዮሐንስ ገብረ እግዚዘብሔር
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ