1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ድርቅ እና የምግብ እጥረት ኢትዮጵያ

ሐሙስ፣ የካቲት 10 2008

በኢትዮጵያ ድርቅ ላስከተለው የምግብ እጥረት መቋቋሚያ ያስፈልጋል ከተባለው 1.4 ቢሊዮን ዶላር እስከ አሁን ከለጋሾች የተገኘው 46 ከመቶ ብቻ ነው ። ቀሪዉ ደግሞ በእትዮጲያ መንግስት እና በተቀሩ ለጋሽ አገሮች እንደሚሸፈን የአደጋ መከላከልና ዝግጁነት እና የምግብ ዋስትና ዘርፍ ኮምሺነር አቶ ምትኩ ካሳ ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል።

https://p.dw.com/p/1HxZG
Äthiopien Hunger Hungerhilfe
ምስል Reuters/T.Negeri

[No title]

ሆኖም ለጋሽ አገሮች የሚጠበቀውን ገንዘብ ካልሰጡ የኢትዮጵያ መንግስት ለልማት ሊያውል ካቀደው ገንዘብ የተወሰነውንም ቢሆን በምግብ እጥረት የተጎዳውን 10.2 ሚሊዮን ህዝብ ለመመገብ ሊጠቀምበት እንደሚችል ጉዳዩን በቅርቡ የሚከታተሉ ያሳስባሉ።

የምግብ እጥረት ጉዳዮችና እና የልማት ባለሙያ አቶ ደሳለኝ ራህማቶ ትልቁን ሸክም የሚርፍበት የእትዮጲያ መንግስት ለልማት ያቀደዉን በጀት በመጠኑም ቢሆን ለዚህ ጉዳይ መጠቀም እንደሚችል ይናገራሉ። መንግስት የጠበቀዉን ያህል የዉጭ ርዳታ ካላገኘ በጀቱን እንደገና ለማጠፍ ሊገደድ እንደሚችልም ጠቁመዋል ። በርሳቸው አባባል ሊታጠፉ የሚችሉት የመንገድ ሥራና ፣ የግድብ ሥራን የመሳሰሉ ብዙ ካፒታል የሚያስፈልጋቸው ፕሮጄክቶች ሊሆኑ ይችላሉ ።

Äthiopien Hunger Hungerhilfe
ምስል picture-alliance/dpa/M. Ayene

ይሁን እንጅ የኢትዮጵያ መንግስት ኮሙኒኬሼን መሥሪያ ቤት ሃላፊ አቶ ጌታቸዉ ረዳ ባለፈዉ ዓርብ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ መንግስት የልማት ስራዎችን ማጠፍ ሳይጠበቅበት ችግሩን ከለጋሽ አገሮች ጋር በመሆን ይፈታል ሲሉ ተናግረዋል።

የብሄራዊ ምቲዮሮሎጂ ኤጅንስ በሰጠዉ ትንብያ መሰረት የበልግ ዝናብ ጥሩ ይሆናል የምል ትንብያ እንዳለም ኮሚሽነር ምትኩ ተናግረዋል ። ስለ ችግሩ በዶቼ ቬሌ የፌስቡክ ደረ ገፅ ላይ በተደረገዉ ዉይይት ላይ የተሳተፉ የተወሰኑ የፌስቡክ ተከታታዮች መንግስት እና ሰብዓዊ ርዳታ የሚሰጡ ድርጅቶች በጋራ ችግሩን መቋቋም እንደሚችሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

Äthiopien Frauen mit Kindern
ምስል Reuters/T. Negeri

በተለይም መጪው የዝናብ ጊዜ የተሻለ ከሆነ ለችግሩም መፍትሄ እንደሚሆን አትተዋል። ይሁን እንጂ ሌሎች መንግስት መድረግ አለበት የሚሉትን በትችት መልክ አቅርበዋል። ከመካከላቸው መንግስት እህል ለውጭ ገበያ ማቅረቡን አቁሞ ምግቡን ለተከሰተው ችግር መቋቋሚያ እንዲያዉል እንዲሁም በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንም በእርዳታ ድያስፖራ ዉስጥ የምገኙት መሳተፍ እንዳለባቸዉም ጠቁመዋል።

መርጋ ዮናስ

ሂሩት መለሰ