1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ደቡብ ሱዳን በሠላም ጎዳና

ዓርብ፣ የካቲት 4 2008

ከዓመታት ዉይይት-መፋረስ፤ ድርድር-መነታረክ በኋላ ባለፈዉ ነሐሴ የተፈረዉ የሠላም ዉል ተፋላሚ ሐይላት እስካለፈዉ ጥር አጋማሽ ድረስ ብሔራዊ የአንድነት መንግስት እንዲመሠርቱ የሚጠይቅ ነበር።ጥር-በየካቲት ተተካ-የወረቀት ላይ ቃል ገቢር አልሆነም።

https://p.dw.com/p/1HuZ9
ምስል Getty Images/AFP/M. Sharma

[No title]

የደቡብ ሱዳን ፕሬዝደንት ሳልቫኪር የቀድሞ ምክትላቸዉን እና የኋላ ጠላታቸዉን ሪክ ማቻርን በምክትል ፕሬዝደንትነት በመሾማቸዉ በጦርነት ለተመሰቃቀለችዉ ሐገር አዲስ ተስፋ ፈንጥቋል።ኪር ዛሬ ያወጁትን ሹመት ተሿሚዉ በደሥታ ተቀብለዉታል።የፕሬዝደንት ኪር መንግሥት እና የማቻር አማፂያን ባለፈዉ ነሐሴ ባደረጉት ሥምምነት መሠረት ተቀናቃኝ ሐይላት ጊዚያዊ የብሔራዊ አንድነት መንግሥት መመሥረት አለባቸዉ።ተፋላሚ ሐይላት የአንድነቱን መንግሥት እንዲመሠርቱ የአፍሪቃ እና የምዕባዉያን መንግሥታት ከፍተኛ ግፊት ሲያደርጉባቸዉ ነበር።ነጋሽ መሐመድ ዝርዝር ዘገባ አለዉ።

ከዓመታት ዉይይት-መፋረስ፤ ድርድር-መነታረክ በኋላ ባለፈዉ ነሐሴ የተፈረዉ የሠላም ዉል ተፋላሚ ሐይላት እስካለፈዉ ጥር አጋማሽ ድረስ ብሔራዊ የአንድነት መንግስት እንዲመሠርቱ የሚጠይቅ ነበር።ጥር-በየካቲት ተተካ-የወረቀት ላይ ቃል ገቢር አልሆነም።በተለይ ፕሬዝደንት ሳልቫኪር ጠቅልለዉ የያዙትን ሥልጣን ለማጋራት የሐይል ሚዛን፤የዉጪ ሐይላትን ግፊትና ጫናን ሲያሰሉ የደጋፊዎቻቸዉን አቋም ሲሰልሉ-ሲያደቡ ነበር።

ኪር የሥምምነቱን ገቢራዊነት ከማጓተት ጋር የአዲሲቱን ሐገራቸዉን ክፍለ-ግዛቶች ከአስር ወደ ሃያ ሥምንት ሸንሽነዉ የተቃዉሞ ጫናዉን ክብደት ጥልቀት ለመለካት ሞክረዉም ነበር።«አልቻሉም» ይላሉ የኢትዮጵያ የሠላምና ልማት ዓለም አቀፍ ጥናት ተቋም አጥኚ አቶ አበበ አይነቴ።

Südsudan Rebellenführer Riek Machar
ምስል Reuters/G. Tomasevic

በተለይ አዲስ አበባ ላይ በቅርቡ በተሠየመዉ የአፍሪቃ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ ላይ የተነገረዉን ማስጠን ቂያ የአዲሲቱ ሐገር መሪ እንደዘበት ማለፍ አልቻሉም።እና አቅማምተዉ ፤ አመንትተዉ ግን ተገደዉ በስተመጨረሻዉ-አደረጉት።«እኔ ሳልቫ ኪር ማያርዲት፤ የደቡብ ሱዳን ሪፐብሊክ ፕሬዝደንት» ይላል ትናንት ማታ በጁባ ቴሌቪዥን የተነበበዉ አዋጅ «ዶክተር ሪክ ማቻር ቴንይ የደቡብ ሱዳን ሪፐብሊክ ተቀዳሚ ምክንትል ፕሬዝደንት ሆነዉ መሾማቸዉን አዉጃለሁ»

አዲስ አበባ እንደሆኑ የሚታመነዉ የእስካሁኑ የአማፂያን መሪ ሪክ ማቸር መሾማቸዉን አስደሳች ብለዉታል።«የሠላም ሥምምነቱን ተግባራዊ ለማድረግ አንድ እርምጃ ነዉ»-አከሉ ማቻር ለዜና ምንጮች።አቶ አበበ አይነቴ እንደሚሉት ደግሞ ሹመቱ ሁለት ነገር ጠቋሚ ነዉ።ፕሬዝደንት ኪር ሪክ ማቻርን ከሥልጣን በማባረራቸዉ ሰበብ የተቀሰቀሰዉ ጦርነት ወትሮም ከጦርነት ያላገገመችዉን ሐገር አዉድሟታል።ሁለቱ ባላንጦች እንደ ቀድሞዉ ሥልጣን ሲጋሩ፤ ሁለት ዓመት በመሩት ጦርነት ያለቀዉን በአስር ሺሕ የሚቆጠር ሕዝብ እየዘከሩ፤ የምግብ እርዳታ የሚያሻዉን 3 ሚሊዮን ሕዝብ እየቆጠሩ መሆን አለበት።

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ