1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

26 ዓመት ያስቆጠረዉ የምሥራቅ ምዕራብ ጀርመን ዉህደትና የመጤዎች ጥላቻ፤

ማክሰኞ፣ መስከረም 24 2009

26 ዓመት ያስቆጠረዉ የምሥራቅ ምዕራብ ጀርመን ዉህደትና በመጤዎች ጥላቻ የጨለመዉ ገፅታ፤

https://p.dw.com/p/2Qq14
Deutschland | Tag der Deutschen Einheit - Dresden 2016
ምስል DW/M. Fürstenau

Bericht zum Stand der deutschen Einheit - MP3-Stereo

የፌደራላዊት ጀርመን የምሥራቅ የሀገሪቱ ክፍል የምክር ቤት አባላት፤ በምሥራቅ ጀርመን አካባቢ ያለዉ የመጤዎች ጥላቻ እና የኤኮኖሚ ልማት ይዞታ እንደሚያሳስባቸዉ እያመለከቱ ነዉ። በተደጋጋሚ በአካባቢዉ ለስደተኞች መጠለያ የተዘጋጁ መኖሪያዎች ላይ የደረሱ ጥቃቶች የምሥራቅ ጀርመንን ገጽታ እንዳደበዘዘዉ የሚያምኑት ባለስልጣናት፤ ያም ሆኖ ግን አዎንታዊ ለዉጦች እየታዩ መሆኑንም ይናገራሉ። 

«ባለፉት 26 ዓመታት ምሥራቅ ጀርመን  ዉስጥ በርካታ ነገሮችን አሳክተናል።» በማለት ነዉ ኢሪስ ግሊክ ስለጀርመን ዉሕደት ይዞታ ዓመታዊ ዘገባ ባቀረቡበት ጊዜ ለጀርመን ምክር ቤት የተናገሩት። ግሊክ የምሥራቅ ጀርመኗ ግዛት ቱሪንገን ተወላጅ ናቸዉ። የ52 ዓመቱ ፖለቲከኛ የሚያሳስባቸዉ፤ ከየትኛዉ የጀርመን ክፍል መገኘታቸዉ ሳይሆን ከኤልበ ወንዝ በስተ ምሥራቅ ባለዉ ማኅበረሰብ ዘንድ በግልፅ እያደገ የመጣዉ ለመጤዎች ጥላቻ ነዉ። ከሕዝቡ ቁጥር አንጻርም ቀኝ አክራሪዎች የሚያደርሱት ጥቃት በፍጥነት እየጨመረ መጥቷል። ቀኝ አክራሪነት፤ የመጤዎች ጥላቻ እና አለመቻቻል በአካባቢዉ የኤኮኖሚ እድገት ላይ በግልፅ አሉታዊ ተጽዕኖ ማሳረፉ እየታየ ነዉ። ይህም የቀጣዩ አደጋ አመላካች ብቻ ሳይሆን የመላዉን ዓለም ትኩረት የሳበ እና ያስደነገጠ ነዉ። ምሥራቅ ጀርመን ዉስጥ ማኅበራዊ ሰላምን ለማረጋገጥ የፖለቲካ እና የሲቪል ማኅበረሰቡ የተቀናጀ ወሳኝ ርምጃ ሊወሰድ ይገባል ቢባልም ግሊክ፤ አብዛኛዉ ምሥራቅ ጀርመናዊ መጤዎችን የሚጠላ እና ቀኝ ፅንፈኛ እንዳልሆነ አስረግጠዉ ያስረዳሉ። ይህ አለ የሚሉት አብላጫ የማኅበረሰብ ክፍልም በግልፅ እና ከፍ ባለ ድምጽ ይህን አቋሙን በይፋ ቢያሳይ ይመኛሉ።

Deutschland | Tag der Deutschen Einheit - Dresden 2016
ምስል DW/M. Fürstenau

"በምሥራቁ ክፍል ልክ እንደ ምዕራቡ ስደተኞችን ለመርዳት የተሰማሩ እጅግ ግሩም፤ በጎ ፈቃደኞች እና የነጻ ተባባሪዎች አሉ። ይህ ገፅታ ባለፉት ጊዜያት በመጤዎች ጥላቻ ምክንያት በተፈጸሙት በርካታ ጥቃቶች መደብዘዝ ብቻም አይደለም፤ እንደዉም በአፍቃሪ ናዚዎች፤ በቀኝ አክራሪዎች እና በመጤ ጠሎች ተጋርዷል።»

ምዕራቡና ምሥራቁ ጀርመን በጋራ ለማደግ ያደረጉት ጠንካራ ጥረት ለስደተኞች መጠለያ የዘጋጁ መኖሪያዎችን በማቃጠል ተጋርዷል። የሥራ አጦች ቁጥር በ9,2 በመቶ ቀንሷል። በምሥራቁ የሀገሪቱ ክፍል ሁለት እጅ እጥፍ የነበረበት የቅርብ ጊዜ ትዉስታ ነዉ። በምዕራብ ጀርመን 5,7 በመቶ ነዉ። ምንም እንኳን ከምዕራቡ ይልቅ በምሥራቅ ጀርመን በመጤዎች ላይ የሚታየዉ ጥላቻ ግልፅ የወጣ ቢሆን፤ ለኤኮኖሚዉ እድገት ይህ ብቻዉን አሉታዊ ጫና አስከትሏል ማለት ግን አይቻልም። ምክንያቱም ስደተኞች በብዛት ወደ ጀርመን ገብተዉ ይህ ቀዉስ ከመባባሱ በፊትም አካባቢዉ በመሠረታዊ ልማት ጉድለት ሲቸገር ቆይቷል። ግሊከ እንደሚሉትም ለዚህም እንቅፋት የሆነዉ ትንሽነቱ ነዉ። የምሥራቅ ጀርመን ማኅበረሰብ ቁጥር እየቀነሰ በመሄዱ እና የተማረ ኃይል እጥረትም በመኖሩ ስደተኞች በማኅበረሰቡ ዉስጥ ተዋህደዉ መኖራቸዉን እንደአንድ ዕድል መጠቀም እንደሚገባም እምነታቸዉ ይገልጻሉ።

«ግባችን ምሥራቅ ጀርመን በስደተኞች የምትወደድ እና እንደ አዲስ ሀገራቸዉ ሊኖሩባት የሚመርጧት ስፍራ እንድትሆን ማድረግ ነዉ። ሊኖሩባት፤ ሊሠሩባት እና በማኅበራዊዉ ዘርፍ ሁሉ አስተፅኦ የሚያበረክቱባት ሀገር።»

Deutschland | Tag der Deutschen Einheit - Dresden 2016
ምስል DW/M. Fürstenau

የምሥራቅ ጀርመን ገጠራማ አካባቢዎችን ይበልጣ ሳቢ ለማድረግም የዲጂታል አገልግሎትን መስፋፋትን ባለስልጣኗ እንደስልት ጠቅሰዋል። ይህም ሰዎች ራሳቸዉን ችለዉ በገለልተኛነት ሥራዎችን ማከናወን እንዲችሉ ይረዳል የሚል ተስፋ አላቸዉ። ከዚህም ሌላ ለታዳሽ የኃይል ምንጭ አቅራቢዎች ሰፊ ዕድል በአካባቢዉ መኖሩንም ጠቁመዋል። ሀገሪቱ በካይ የኃይል ምንጭ ከሆነዉ ቀስ በቀስ ለመላቀቅ ያደረገችዉ ጥረት በአካባቢዉ የበርካቶችን የሥራ አሳጥቷል።

ማርሰል ፉርስተናዉ/ ሸዋዬ ለገሠ

ኂሩት መለሰ