የዩናይድ ስቴትስና የሰሜን ኮሪያ ፉከራ
ዓርብ፣ ነሐሴ 5 2009ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ፒዮንግያንግ በጅልነት የምትለዉን አሜሪካን ላይ ተግባራዊ ለማድረግ ብትሞክር ወታደራዊ መፍትሄዉ ሙሉ በሙሉ መዘጋጀቱን በትዊተር መልዕክታቸዉ ጠቁመዋል። የአሜሪካን የመከላከያ ሚኒስትር ጀምስ ማቲስ በበኩላቸዉ ምንም እንኳን የእሳቸዉ ኃላፊነት ወታደራዊ ተልዕኮዉን ማስፈፀም ቢሆንም ቀዉሱን በዲፕሎማሲ መፍታት ይቻላል የሚል ተስፋቸዉ እንዳልተማጠጠ ተናግረዋል። የቃላት ጦርነቱ እየናረ በሄደበት በዚህ ወቅት ሰሜን ኮርያ አራት ሚሳኤሎችን ወደ አሜሪካኗ ጉዋም ግዛት ለመተኮስ ዝግጅቴን አጠናቅቄያለሁ እያለች ነዉ። በጉዋም የባህር ዳርቻ የሚገኙ ነዋሪዎች ይህን ዜና ከሰሙ በኋላ አስተያየታቸዉን እንዲህ ሰጥተዋል፤
«እንዲህ ያለዉን ዛቻ ለምደነዋል፤ በቦምብ እንደምንመታም በየጊዜዉ እንሰማለን ግን ሆኖ አያዉቅም። አሁን ደግሞ በድጋሚ እየሰማን ነዉ። እናም ለእኛ አዲስ ነገር አይደለም።»
«ሆኖ አያዉቅም፤ እናም ምን ስጋት አልገባኝም። ምናልባት ማደናቀፊያ ነገር ሊሆን ይችላል። ምናልባትም የፖለቲካ ርምጃ አይነት ይሆናል፤ ማለት፤ በዩናይትድ ስቴት እና በኮሪያ በኩል ምናልባት ትኩረት ለማግኘት የመፈለግ አይነት ይሆናል።»
ሚሳኤል ያነጣጠረባት የጉዋም ነዋሪዎች ጉዳዩን አቅልለዉ ቢያዩትም፤ የተለያዩ የምዕራብ ሃገራት መሪዎች ግን ወታደራዊዉ ዛቻ ስጋት የፈጠረባቸዉ መስሏል። የጀርመን መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል የተካረረዉን ዉጥረት በጦር መሣሪያ መፍታት እንደማይቻል ሲያሳስቡ፤ ሩሲያ በበኩሏ እሰጥ አገባዉ ከመጠን ማለፉን በመጥቀስ የሁለቱ ሃገራት መሪዎች ወደቀልባቸዉ እንዲመለሱ ጠይቃለች።
የፖለቲካ ተንታኞች ግን የሁለቱ ሐገራት መሪዎች አንዱ ሌላዉን ከማስፈራራት አልፈዉ ዉጊያ መግጠማቸዉን ይጠራጠራሉ። አንድ ኢትዮጵያዊ የሕግ ምሑር በበኩላቸዉ ሰሜን ኮሪያ ዉጊያ ከጀመረች ከፍተኛ ጥፋት ይደርስባታል።» ይላሉ። ይሁንና ያሁኑ ዉጥረት የኑክሌር ቦምብ ዉጊያ ማስከተሉን ይጠራጠራሉ። የዋሽግተን ዲሲዉ ወኪላችን መክብብ ሸዋ ዝርዝር ዘገባ ልኮልናል።
መክብብ ሸዋ
ነጋሽ መሐመድ
ኂሩት መለሰ