1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የየመኑ ጦርነትና የሕዝቡ መከራ

ሐሙስ፣ ሰኔ 25 2007

ከአደን ሁለት መቶ ኪሎ ሜትር ረቀት ላይ አንድ የባሕር ወሽመጥ አለ። ቀይ ባሕር እና የአደን ባሕረ ሠላጤ ወይም ሕንድ ዉቅያኖስ የሚለያዩበት። ባብ አል መዳብ አሉት የጥንት አረቦች። የእንባ በር። አደን-የመን።

https://p.dw.com/p/1Frsz
ምስል picture-alliance/dpa

ሁቲ የተሰኘዉ የየመን አማፂ ቡድን እና ከሐገር የተሰደደዉ መንግሥት ደጋፊዎች በሐገሪቱ ሁለተኛ እና ሠወስተኛ ትላልቅ ከተሞች የገጠሙት ጦርነት ዛሬም እንደቀጠለ ነዉ። ትናንት በሁለተኛይቱ ትልቅ ከተማ አደን በተደረገዉ ዉጊያ በትንሽ ግምት ሠላሳ-አምስት ሠላማዊ ሰዎች ተገድለዋል። ከአንድ መቶ በላይ ቆስለዋል። በሐገሪቱ ሰወስተኛ ትልቅ ከተማ ተኢዝ ዉስጥ በሚደረገዉ ዉጊያ መሐል በሺሕ የሚቆጠሩ እስረኞች አምልጠዋል። ስደተኛዉን መንግሥት የሚደግፈዉ ሳዑዲ አረቢያ መራሹ ጦር «የሁቲዎች ይዞታ» የሚለዉን አካባቢ መደብደቡም እንደቀጠለ ነዉ። ጦርነቱ አብዛኛዉን የሐገሪቱን ሕዝብ ለረሐብ አጋልጧል። ነጋሽ መሐመድ የዜና መልዕክቶችን እንደሚከተለዉ አሰባስቧል።

ያዩ እንደሚሉት ያቺ ጥንታዊ፤ ደማቅ፤ ከተማ ፤ ባሕር ተንተርሳ፤ ዉሐ ተጫምታ ዉሐ ይጠምታል። በወደቦች ተሞልታ-ትራባለች። መዉጪያ፤ መግቢያ አጥታ ታፍናለች። አደን። ድምቀት-ዉበቷ ረግፏል። በዚያ ላይ ከሰማይ የአዉሮፕላን፤ ከምድር የእጅ-የትከሻ ቦምብ ሚሳዬል፤ ጥይት ይዘንብባታል። አደን። ትናንት።

አደን የሚኖሩት ኢትዮጵያዊ። ዛሬም ቀጥላለች። የቆሰሉት ሰዎች ቁጥር አንድ መቶ መድረሱን የከተማይቱ የጤና ባለሙያዎች አስታዉቀዋል። ሳዑዲ አረቢያ በስደት የሚኖሩትን ፕሬዝደንት አብድረቦ መንሱር ሐዲን የሚደግፈዉ ሳዑዲ አረቢያ መራሹ ጦር ጄቶች ባንፃሩ አደን አጠገብ የሚገኙ ሰወስት መንደሮችን ደብድበዋል። አስራ-ሰወስት ሰዎች ተገድለዋል።

Jemen Tais Anti-Huthi Demonstration
ምስል Reuters/A. Mahyoub

የየመንዋ ሰወስተኛ ትልቅ ከተማ ታኢዝም ትናንት ስታጋይ ነዉ የዋለችዉ። የጦርነቱ ድል አድራጊዎች እስካሁን እስረኞች ናቸዉ። ከ1,200 የሚበልጡ እስረኞች በዉጊያ ትርምሱ መሐል ተሠዉረዋል። ከእስረኞቹ መሐል በዓለም አቀፉ አሸባሪ ድርጅት አል ቃኢዳ አባልነት የሚጠረጠሩ አሉበት።

ጦርነቱ ሰነዓ፤ ዓደን፤ ተኢዝ፤ ሰዓድ ይሁን ሌላ ሥፍራ በሠላማዊዉ ሕዝብ ላይ የሚያደርሰዉ ስቃይ ከጊዜ ወደጊዜ እየከፋ ነዉ። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እንደሚለዉ ሰማንያ ከመቶ የሚሆነዉ ወይም ከ21 ሚሊዮን የሚበልጠዉ የየመን ሕዝብ አስቸኳይ ርዳታ ያስፈልገዋል።

ዓለም አቀፉ ድርጅት አንድ ዓይነት ዘገባዉን እየደገመ፤ እያሰለሰ፤ እየመላለሰ ሰሚዉን ከማሰልቸት ባለፍ እስካሁን ለተቸገረዉ ሕዝብ ምናምኒት የሰጠዉ የለም።

በሠላሙ ጊዜ ከሥድስት መቶ ሺሕ እስከ ሰባት መቶ ሺሕ የሚገመት ነዋሪ፤ ከሁለት እስከ ሰወስት መቶ ሺሕ የሚገመት የዉጪ ስደተኛ፤ ሠራተኛ፤ ሐገር ጎብኚ ይኖርባት ነበር። በቅርቡ በተለይ ሳዑዲ አረቢያ መራሹ ጦር የመንን መደብደብ ከጀመረበት ካለፈዉ መጋቢት ወዲሕ አብዛኛ ነዋሪ፤ስደተኛ፤ ሠራተኛዋ ጥሏት ወጥቷል። ኦና ቀርታለች።

እስካሁን ከተማይቱን ለቀዉ መዉጣት ያልቻሉት ዉሐና መብራት ጭል ጭል በሚልበት መንደር ሠፍረዋል። ግን ጦርነቱ እዚያም ተከትሏቸዉ መጣ።

Bab al-Mandab (Eingang zum Roten Meer)
ምስል picture alliance/Photoshot/BCI

አደን የሚኖሩት ኢትዮጵያዊያን ሐገራቸዉ ለመመለስ የኢትዮጵያ መንግሥት መርከብ እስኪልክላቸዉ እየጠበቁ ነዉ። እስከ መቼ አይታወቅም። የሚታወቀዉ መመለሻቸዉን ከሚያሰላስሉት ስደተኞች መሐል የተወሰኑት የሚሳዬል ማብረጃ መሆናቸዉ ነዉ።

ከአደን ሁለት መቶ ኪሎ ሜትር ረቀት ላይ አንድ የባሕር ወሽመጥ አለ። ቀይ ባሕር እና የአደን ባሕረ ሠላጤ ወይም ሕንድ ዉቅያኖስ የሚለያዩበት። ባብ አል መዳብ አሉት የጥንት አረቦች። የእንባ በር። አደን-የመን።

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ

 

 

 

 

 

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ