የኦባማ ጉብኝትና የኢትዮጵያ ወጣቶች
ዓርብ፣ ሐምሌ 24 2007ከአንድ ቢሊዮን በላይ ህዝብን በሚወክለው የአፍሪቃ ህብረት አዳራሽ ማክሰኞ ዕለት ንግግር ያሰሙት የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦማባ፤ «ኃይል እና በጎ መንፈስ የተሞሉ በርካታ ወጣቶችን በዛሬይቱ አፍሪቃ በማየቴ ደስ ብሎኛል» ሲሉ ተሰምተዋል። ወጣቱስ በፕሬዚዳንቱ ጉብኝት በተለይም ንግግር ምን ያህል ደስተኛ ነበር?
የአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪ የሆነው ወጣት ቢንያም፤ ለምሳሌ በፕሬዚዳንት ኦባማ ጉብኝት ተደስቷል። ኦባማ ሸማቂ ቡድን አሸባብን በመዋጋቱ ረገድ የተናገሩትንም አስደስቶታል።ኦባማ አሸባብን በመዋጋቱ ረገድ ስለ ኢትዮጵያ ጦር የተናገሩት ጥሩ ሆኖ ሳለ፤ ሸክሙ በኢትዮጵያ ጦር ላይ ብቻ ባይሆን ጥሩ ነው ይላል ወጣት ደሴ በበኩሉ።
ይሁንና ከፕሬዚዳንት ኦባማ ጋዜጣዊ መግለጫዎች የጠበቀችው እና ሆኖ ያገኘችው ያልተጣጣሙላት፤ የአዲስ አበባ ወጣት ሀናም ፤ ምክንያቷን ገልፃልናለች። ሀና ብቻ ሳትሆን በተለይ ፕሬዚዳንት ኦባማ ሰኞ ዕለት ከጠቅላይ ሚኒስትር ሐይለማሪያም ደሳለኝ ጋር በጋራ የሰጡትን ጋዜጣዊ መግለጫ የተከታተሉ የፌስ ቡክ ታዳሚዎቻችን በጋዜጣዊ መግለጫው እንዳልተደሰቱ ነበር ያካፈሉን። የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ጉዳይ፤ ሀሳብን በነፃ መግለፅ እና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ አካሄድ ለበርካቶች እንደጠበቁት ያልተወሱ ብሎም በወጉ ያልተነሱ ርዕሶች ነበሩ። ኦባማ በአፍሪቃ ህብረት ለአፍሪቃ መሪዎች ያነሱት አንድ ነገር ተሰሚነት ካገኘ እጅግ አስደስቶኛል ይላል ደሴ። እንዲሁም ጨርሶ የኦባማ ወደ ኢትዮጵያ መምጣትን የተቃወመው የባህር ዳር ነዋሪ ወጣት አማኑኤል አስተያየትም አለን። ሁሉንም በድምፅ ያገኛሉ።
ልደት አበበ
ሸዋዬ ለገሠ