1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኦባማ እና የሜርክል ግንኙነት

ረቡዕ፣ ኅዳር 7 2009

የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚደንት ባራክ ኦባማ ለሁለት ቀናት ጉብኝት ዛሬ በርሊን ይገባሉ። የጀርመን መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል የስልጣን ዘመናቸውን በቅርቡ የሚያበቁትን አሜሪካዊው ፕሬዚደንት ማምሻቸውን በጽሕፈት ቤታቸው ይቀበላሉ።

https://p.dw.com/p/2SmtI
Deutschland - NATO Gipfel mit Barack Obama und Angela Merkel
ምስል picture-alliance/dpa/J. Koch

for cms Obama Merkel - MP3-Stereo

የጀርመን መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል የስልጣን ዘመናቸውን በቅርቡ የሚያበቁትን አሜሪካዊው ፕሬዚደንት ማምሻቸውን በጽሕፈት ቤታቸው ይቀበላሉ። 

ባራክ ኦባማ እጎአ በ2008 ዓም የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚደንት ሆነው መመረጣቸውን ጀርመናውያን በደስታ ነበር የተቀበሉት። መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ግን ፕሬዚደንታዊው ዕጩ ኦባማ በምርጫ ዘመቻ ወቅት በታወቀው የብራንድንቡርግ በር ላይ  ንግግር ለማሰማት ያቀረቡትን  ጥያቄ መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ውድቅ በማድረግ ፊት ነስተዋቸው እንደነበር አይዘነጋም። በዚሁ የሜርክል ውሳኔ ሰበብ  ሁለቱ መሪዎች የተቀራራበ ግንኙነት እስኪፈጥሩ ድረስ ጥቂት ጊዜ ማለፍ ነበረበት።  

Bundeskanzlerin Merkel NSA Überwachung Obama
ምስል SAUL LOEB/AFP/Getty Images

ፕሬዚደንታዊው ዕጩ ኦባማ  ያኔ ዲስኩራቸውን እንደ ሁለተኛ ኬኔዲ እና የጆርጅ ዳብልዩ ቡሽ ዘመነ ስልጣንን የሚያበቁለት አድርጎ ለተመለከታቸው 200,000 ሰው ያሰሙት  ከነፃነት አደባባይ ነበር። ቡሽ በኢራቅ ጦርነት ሰበብ በዩኤስ እና በከፊል አውሮጳ መካካል ልዩነት ተፈጥሮ ነበር። በዚያን ጊዜ በሶሻል ዴሞክራቱ ጌርሀርት ሽረደር ይመራ የነበረው የጀርመን መንግሥት የኢራቅን ጦርነት ሲቃወም፣ የተቃዋሚው ክርስትያን ዴሞክራቶቹ ህብረት መሪ የነበሩት አንጌላ ሜርክል ከቡሹ ጎን ነበር የተሰለፉት።  
ኦባማ በመጀመሪያው የስልጣን ዓመት 2009  ምንም እንኳን ሁለቴ ወደ ጀርመን ቢመጡም፣ በርሊንን ከመጎብኘት ተቆጥበዋል። ይህም ቅሬታ መፍጠሩ አልቀረም። ከዚያ በቀጠሉት ዓመታትም የሜርክል እና የኦባማ ግንኙነት እንደተቀዛቀዘ ነበር የቀጠለው። ለዚህም፣ እንደ ይላሉ የጀርመን የውጭ ፖለቲካ ድርጅት የዩኤስ አሜሪካ አዋቂ ዮሴፍ ብራምል አስተያየት፣ ተጨባጭ ምክንያቶች ነበሩ፣ 
«  በሀገር ውስጥ ችግሮች የተወጠሩት ኦባማ በፀጥታ ጥበቃው እና በኤኮኖሚው ፖሊሲ፣ እኛ ላይ ፍፁም የማይጥመንን ሸክም ስለጫኑብን በርሳቸው አመራር ስር ግዙፍ ችግሮች ነበሩብን። »
በዚህ የተነሳ ኦባማ ለመራሒተ መንግሥት ሜርክል አንድ የውጭ ዜጋ ሊሰጥ የሚችለውን ከፍተኛውን የሀገሪቱን  በ2011 ዓም የነፃነት ሜዳልያን አበርክተዋል። ይህን ርምጃቸውን ታዛቢዎች እንደ እርቀ ሰላም ርምጃ ወይም ተጨማሪ ኃላፊነት እንዲወስዱ ለመገፋፋት የወሰዱት አድርገው ተመልክተውታል።   
ኦባማ በ 2013 ዓም በብራንድንቡርግ በር ዲስኩር ሲያሰሙ፣ በዚያን ወቅት ሜርክል እና እሳቸው አንድነታቸውን ማጉላት ችለው ነበር፣ ግን ወዲያው «ኤን ኤስ ኤ» በተባለው የአሜሪካውያን ስለላ ድርጅት ተግባርሰበብ ፣ በተለይም፣ የሜርክልን የእጅ ስልክ ሳይቀር የሰለለበት ተግባር  የተነሳ በሁለቱ ግንኙነት ላይ ቅሬታ ፈጥሮዋል፣ ሜርክል ድርጊቱን በጥብቅ ቢነቅፉም፣ ፖለቲካዊ  ርምጃ ሳይወስዱ ነው ያለፉት።   ኦባማ እና ሜርክል ዓመታት በለፉ ቁጥር በፖለቲካው እና በግል ግንኙነታቸው እየተቀራረቡ መምጣታቸውን በሜርክል የክርስትያን ዴሞክራቶች ህብረት ከአትላንቲክ ባሻገር ያለው ግንኙነት ደጋፊ ፔተር ቤየር ገልጸዋል።
« ኦባማ የሜርክልን፣ በተለይም፣  የተግባር ሰውነታቸውን፣ አስተማማኝነታቸውን እና የአመራር ብቃታቸውን  ያደንቃሉ። »
የጀርመን ፖለቲካ እና ኤኮኖሚያዊ አቋም ከፍ እያለ መሄዱ ሲታሰብም ኦባማ የሜርክልን ሚና በቀላሉ ሊያልፉት እንደማይችሉ ቤየር አክለው አስረድተዋል።
ከቡድን ሰባት ጉባዔ በኋላ ሜርክል የሀገራቸውን ድንበር ለስደተኞች የከፈቱበትን ድርጊት፣ ምንም እንኳን ብዙ ጀርመናውያንን ቢያስቆጣም፣  ኦባማ እጅግ ነበር ያደነቁት።  ይሁንና፣ ዩኤስ አሜሪካ ስደተኞችን በመቀበሉ ድርጊት የምትከተለው ፖሊሲ፣ በተጨባጭ ሲታይ ትብብርን ያጎላ አይደለም ያሉት ፔተር ብራምል የኦባማን አድናቆት የማይታመን ሲሉ ቢነቅፉም፣ ኦባማ  በተለይ የስዩሙ የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ ምርጫ በአጋሮቻቸው ላይ ያሳደራል ተብሎ የሚታሰበውን ተፅዕኖ የማረጋጋት ኃላፊነት እንዳለባቸው ስለሚሰማቸው በስንብት ጉዟቸው ከሜርክል ጋር መገናኘታቸው ትልቅ ትርጓሜ ይዞዋል።

Bildergalerie Politiker Gestik Obama und Merkel am Brandenburger Tor 19.06.2013
ምስል Christof Stache/AFP/Getty Images

ክሪስቶፍ ሀስልባኽ/አርያም ተክሌ

ነጋሽ መሀመድ