የኦሕዴድና ኦዴግ የመጀመርያ ዉይይት
ሰኞ፣ ግንቦት 27 2010የኦሕዴድ ምክትል ሊቀመንበርና የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ ለማ መገርሳ ድርጅታቸዉ ለፓርቲዎች «ኑ እንወያይ» ሲል ያቀረበዉን ጥያቄ ኦዴግ መቀበሉን ትላንት በተደረገዉ ዉይይት ላይ አመስገነዋል። አቶ ለማ መገርሳም ከፓርቲዉ ጋር አብሮ ለመስራት ያላቸዉን ፍላጎት ከገለፁ በኋላም በክልሉም ሆነ በሀገሪቱ የፖለትካ ቀዉሱ ስላሳደረው ተፅእኖ መናገራቸዉን የሀገርር ዉስጥ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።
አቶ ለማ: «ዛሬ ባለንበት ወቅት በአገርቱ ዉስጥ የተደራጁት የፖለትካ ፓርትዎች ሁሉ አንድ ላይ መጥተው መወያየት አለባቸዉ። ከጥላቻ ፖለቲካ ዉስጥ ወተን እንደ ሌሎቹ የበለፀጉት አገራት አንድ ላይ ቁጭ ብለን የምንወያይበትና ፤ ልዩነታችንን የምንፈታበት አካሄድ መጀመር አለብን። በዚህ አገር ዉስጥ ከረሃብ በላይ የሰዉን ሕይወት የጨረሰዉ ፖለቲካ ነዉ። የዚህ አጋር ፖለትካ የሰዉን ሕይወት ብቻ አይደለም የጨረሰዉ፤ ብሩህ የሆነ ሰዉ፤ ረጅም ረዕይ ያለዉ ሰው ነዉ በዚህ ፖለትካ የተበላዉ። መቼ ነዉ ይህን ታሪክ የምንቀይረዉ? እኛ የምንፈልገዉ ይህ ታሪክ እንዲለወጥ ነዉ።»
አቶ ሌንጮ ለታና ሌሎች የኦዴግ አመራሮች ለህዝብ ሲሉ ከፍተኛ መስዋዕትነት በመክፈላቸዉ ከፍተኛ አክብሮት እንዳላቸዉ አቶ ለማ መናገራቸዉን ዘገባዉ ጠቅሷል። የኦዴግ ፕሬዝዳንት አቶ ሌንጮ ላታም በማህበረሰቡ መካከል ተገኝተው፤ አብረው ታግለው፤ የሚያስፈልገዉን መስዋዕትነት ከፍለው የሕዝቡን መብት የማስከበር ድርሻቸዉን መወጣት እንደሚፈልጉ መናገራቸዉን ዘገባዉ አክሎ ገልጿል።
አቶ ሌንጮ ለታና: «መጣን፤ ለምን መጣን? አሁን ያለንበት ሁኔታ፤ ኢየተደረገ ያለዉን ለዉጥ እዉን ለማድረግ፣ የምንችለዉን ለማበርከት ነዉ የመጣነዉ። እንደ በፊቱ እንደ ፖለቲካ ፓርቲ ብቻ ለመሥራት አይደለም አመጣጣችን፤ ወሳኙ ነገር አሁን የተጀመረው ለዉጥ ግቡን እንዲመታ ማድረግ ነው።»
የኦሕዴድ፤ የኦዴግ፤ የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስና የኦሮሞ ነፃ አውጭ ግንባር መሠረታቸዉ የኦሮሞ ሕዝብ መሆኑን በትላንትናዉ እለት የክልሉ የኮሙኒኬሼን ጉዳዮች ሀላፊ ዶክተር ነገሪ ሌንጮ በፌስቡክ ገፃቸዉ ገልፀዋል። የኦሮሞ ነጻነትና አንድነት የሚያስማማቸው ከሆነ የማያግባባቸው ነገር ሊኖር እንደማይችል የጠቀሱት ዶክተር ነገሪ አሁንም የተቀሩት የኦሮሞ ታጋዮች ወደ ዉይይት መድረክ እንዲመጡ ጥሪ አቅርበዋል።
ከዚህ በፊት «በጠላትነት ስተያዩ የነበሩ»፤ የተለየ አመለካከት የነበራቸዉ ሃይሎች ህዝብ ፊት ተሰብስበው መናገር መጀመራቸዉ እንደሚበረታታ አምስተርዳም ነዋሪ የኾኑት የኦሮሞ መብት አቀንቃኙ አቶ ገረሱ ቱፋ ተናግረዋል።
አቶ ሌንጮ ባቲ የኦዴግ ቃል አቀባይ «መንግስት የኦሮሞ ነፃ አውጭ ግንባር ወታደሮችንና አባሎችን ከእስር ለመልቀቅና ፣ ደብዛቸው የጠፋ ሰዎችን ጉዳይ ለመመርመር ኮሚቴ ለማቋቋም መስማማቱን ገልፀዋል።
ገዥዉ ፓርቲ በሚቀጥሉት ወራቶች ዉስጥ የፖለቲካ አመራሮችን እና አባላትን ማሰር ማቆም፤ አፋኝ ህጎችን መሰረዝ፤ እንዲሁም ሌሎች የፖለቲካና እኮኖሚ ችግሮች መፍታት መቻል እንዳለበት አቶ ገረሱ አሳስበዋል።
መርጋ ዮናስ
ሂሩት መለሰ