1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢየሩሳሌም የወጣቶች ባንድ

ዓርብ፣ መጋቢት 23 2008

በመካከለኛው ምሥራቅ ሙስሊም ፣ ክርስትያን እና አይሁዳውያን አብረው ይዘፍናሉ ቢባል በአካባቢው ከሚካሄደው ጦርነት ጋር አብሮ ላይሄድልን ይችላል። ምንም እንኳን ፈታኝ ቢሆንም « ኢየሩሳሌም ዩዝ ኮር» የሚባል አንድ የወጣቶች የሙዚቃ ቡድን ውስጥ የተወሰኑ ወጣቶች አብረው ይዘፍናሉ።

https://p.dw.com/p/1INTS
Jerusalem Altstadt mit dem Felsendom
ምስል picture-alliance/dpa/B. Weissbrod

የኢየሩሳሌም የወጣቶች ባንድ

እስራኤል ውስጥ በወጣት ፍልስጤማውያን እና የእስራኤል ፖሊስ መካከል በተደጋጋሚ ግጭት ተስተውሏል። ግጭቱ እንደ ኢየሩሳሌም ባሉ አንዳንድ የአምልኮ ስፍራዎች ሳይቀር ይካሄዳል። ኢየሩሳሌም መፍትሄ ካጣችለት የአይሁድ ፍልስጤም ግጭት ጋር ስትታገል « የሚቻ ሄንድለር የሙዚቃ ቡድን ግን የተሳካለት ይመስላል። ወጣት አይሁዳውያን፣ ክርስትያን እና ሙስሊሞች በሳምንት አንድ ቀን አብረው ሙዚቃ ለመጫወት ይገናኛሉ። የሙዚቃ ቡድኑ መሪ ሄንድለር ከሶስት ዓመት በፊት ነው ይህንን ፕሮጀክት የጀመሩት። በቡድኑ ከተለያዩ ከተማ የተሰበሰቡ ተማሪዎች ይገኙበታል።« ምክንያቱም ይህ ቤታቸው ነው ። አለቀ! ይህ ደህንነት የሚሰማቸው ቦታ ነው። ፍቅር የሚያገኙበት ፣የተሰማቸውን የሚገልጹበት፣ እና ደስታ የሚሰጣቸው ስፍራ ነዉ። ማንነታቸውን በተቀበሏቸው ጓደኞቻቸው ድጋፍ ማግኘት ይችላሉ።»
ወጣቶቹ ልምምድ ከመጀመራቸው አስቀድሞ ሄንድለር የድምፅ ቅላፄዎችን፣ በምዕራብ እና በምሥራቁ ክፍል ስላለው የሙዚቃ የአተረጓጎም ልዩነት እና የመሳሰሉትን ለወጣቶቹ ያብራራሉ። አሜሪካዊው ሄንድለር እንግሊዘኛ ፣ አረብኛ እና እብራይስጥ ይናገራሉ። ይህም የሁሉንም ባህል እኩል ለማስተናገድ እንዲቻል አስፈላጊ ነው ይላሉ አሰልጣኙ። ለምሳሌ ልክ እንደ ኢላይ ኤታን እና ሊሞር« ኢላይ ኤታን እባላለሁ። የምኖረው ፒሲጋት ዜፍ ኢየሩሳሌም ውስጥ ነው። ወደዚህ የሙዚቃ ቡድን ከመጣሁ ስድስት ወር ሆነኝ። ሌላ የትም ቦታ የማላገኘው ልዩ አጋጣሚ ነው።»
ትላለች ኢላይ በእብራይስጥ። አረብኛ ተናጋሪ የሆነችው ሊሞር ደግሞ« ሊሞር እባላለሁ። 16 ዓመቴ ነው። ላለፉት ሶስት ዓመታት እዚህ አብሬ እዘፍናለሁ። የመጣሁት ከቤት ዛፋፋ ነው።»
ኢላይ ኤታን እና ሊሞር ኢየሩሳሌም ውስጥ ላለው አስቸጋሪ ሁኔታ ማሳያ ሊሆኑ ይችላሉ። ኢላይ ኤታን የምትኖርበት ፒስጋት ዜፍ ፍልስጤማውያን የሚኖሩበት አካባቢ ነው። ሊሞር ደግሞ አረቦች ከሚኖርበት የከተማዋ ምሥራቃዊ ክፍል ነው። ወጣቷ ፍልስጤማዊ ናት። ስትወለድ እናቷን የረዷት ሀኪም እስራኤላዊ ስለነበሩ የሳቸውን የአይሁዳውያን ስም ሰጥተዋታል። እስራኤል ምሥራቅ እየሩሳሌምን ከተቆጣጠረች አንስቶ በአካባቢው በተደጋጋሚ ግጭቶች ተከስተዋል። ባለፈው እስራኤላያን አዲስ ዓመትን ሊያከብሩ በዝግጅት ላይ በነበሩበት ወቅት የእስራኤል ፖሊስና ሙስሊም ወጣቶች ኢየሩሳሌም ከተማ በሚገኘው የአል-አቅሳ መስጊድ መጋጨታቸው ይታወሳል። የአል-አቅሳ መስጊድ የሚገኝበት ስፍራ ለክርስቲያኖች፤ ለሙስሊሞችም ይሁን ለአይሁዳውያን ሃይማኖታዊ ክብደት የሚሰጠው ስፍራ ነው።
ዛሬ በሚቻህ ሄንድለር የሙዚቃ አዳራሽ ለመጫወት የተሰበሰቡት 19 ተማሪዎች ሙስሊም እና ክርስትያን ናቸው። እያንዳንዳቸዉ ኢየሩሳሌምን በሚመለከት የየራሳቸዉ ችግር አላቸው። የኢየሩሳሌም ግጭት አልተቋጨም። በአንድ በኩል ወጣት ፍልስጤማውያን በእስራኤላውያን ላይ ስለት ሲመዙ በሌላ በኩል ደግሞ የእስራኤል ፖሊስ ያለ ርህራሄ በፍልስጤማውያን ላይ ይተኩሳል። እአአ ከጥቅምት ወር 2015 ዓም አንስቶ በእስራኤላውያን እና ፍልስጤማውያን መካከል በተቀሰቀሰው ግጭት ከ 90 በላይ ፍልስጤማውያን ሲገደሉ፤ የ 16 እስራኤላውያን፣ አንድ አሜሪካዊ እና አንድ ኤርትራዊም ህይወት ጠፍቷል። ስለሆነም በከተማዋ ያለው ስሜት ልክ እንደ ፀጥታው ሁኔታ ያልተረጋጋ ነው።«አዲስ በተቀሰቀሰዉ ግጭት ምክንያት ነገሮች በእርግጥም ከባድ እንደሆኑ ግልፅ ነው። ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይጠበቅብናል። አንዳንድ ጊዜም ወላጆች ልጆቻቸውን ለልምምድ ወደዚህ ሲልኩ ስጋት እንዳይሰማቸው ከነሱ ጋር በደንብ መወያየት አለብን። ይህ ቦታ አስተማማኝ ሳይሆን ቀርቶ ሳይሆን ከቤትም ወደትምህርት ቤት ሄዶ ለመምጣትም ሁኔታው ለሁሉም አስተማማኝ ባለመሆኑ ነው።ስለዚህ በሁለቱም ወገን ያሉ ወላጆች ልጆቻቸው ጨርሶ ምንም ነገር ለማድረግ ከቤት መውጣታቸው ያሰጋቸዋል።»
ሁኔታው ለማንም ቢሆን አስጊ ነው። እያንዳንዱም ተማሪ የሚያሰጋው የራሱ የሆነ ምክንያት አለው። ፍልስጤማዊቷ ሊሞርን ለምሳሌ የእስራኤል ጦር ፍልስጤማውያንን ሲያስር ወይም አንድ አይሁድ አንድ አረብን ሲገድል መመልከቱም ሆነ መስማቱ ያስጨንቃታል። ወይም ደግሞ ትላለች፤ « ወይም ደግሞ እኔን ኬላ ላይ አስቁመው አረብ ስለሆንኩ ብቻ ሲፈትሹኝ፤ ይህ ደስ የማይል ነገር ስለሆነ ለምን እንዲህ ያደርጉኛል ስል ራሴን እጠይቃለሁ።»
በፒስጋት ዜፍ የምትኖረው ኢላይ በከተማዉ ቀላል ባቡር ተሳፍራ ለልምምድ ወደ ሙዚቃ ባንዱ ስትሄት፤ ሊሞር ግን ከቤት ዛፋፋ የእስራኤልን የቁጥጥር ኬላ አልፎ መጓዝ ይጠበቅበታል። ምንም እንኳን በመጨረሻም ወጣቶቹ አንድ ላይ ተገናኝተዉ ቢዉሉም የሚያጋጥማቸዉ ችግር ግን ይለያያል።
ወጣቶቹ በህብረት ዘፍነው ሲጨርሱም አብዛኛውን ጊዜ አማካሪዎች ከነሱ ጋር ስለዉሏቸዉና ተሞክሮዋቸው ይወያያሉ። ውይይቱም ቡድኑን ለማጠናከርና ወጣቶቹንም ለማቀራረብ ረድቷል። የ« ኢየሩሳሌም ዩዝ ኮር» የሙዚቃ ቡድን ወደ ዩናይትድ ስቴትስ ተጉዞም ዝግጅቱን አሳይቷል። የቡድኑ ቀጣይ ጉዞ ወደ ጃፓን ይሆናል።

Israel Jerusalem Messerattacke auf israelische Soldaten
ምስል Reuters/A. Awad

ቶርስትን ታይሽማ/ ልደት አበበ

አርያም ተክሌ