የኢትዮጵያዉያን ስደተኞች ስቃይ በግብፅ
ዓርብ፣ ሐምሌ 15 2008
«UNHCR» በበኩሉ ችግሩን ለመቅረፍ ከኦሮሞ ማኅበረሰብ መሪዎች ጋር እየተወያየ እንደሆነ ገልጿል።
በግብፅ የሚገኘዉ የስደተኞች ከፍተኛ ኰሚሽን «UNHCR» ቢሮ በተለይ የኦሮሞ ስደተኞችን ጥያቄ ዉድቅ እያደረገ በመሆኑ፤ ተገን ጠያቂዎቹ ዉሳኔዉን በተለያዩ ተቃዉሞዎች ቢገልጹም የሚሰማቸዉ እንደጠፋ ይናገራሉ። ትናንት ኃሙስ ሁለት ስደተኞችጠያቂዎች ራሳቸዉን በእሳት እንዳቃጠሉ የሚናገሩት፤ በአርሲ ዩንቨርስቲ የሥነ-ጽሑፍ መምህር የነበሩትና በአሁኑ ወቅት በካይሮ የኦሮሞ ማኅበረሰብ አስተባባሪ አቶ ያዘዉ ከበበ እንደሚሉት፤ ባለፈዉ ሁለት ወራት ብቻ 120 ኦሮሞዎች ሆነ ተብሎ በስደተኞች ከፍተኛ ኰሚሽን ጥያቄያቸዉ ታግዶአል። ተቀባይነት ለተነፈጉት ለነዚህ ሁሉ ስደተኞች የተሰጠዉ የምክንያት ዝርዝር ከስም ዉጭ አንድ አይነት ነዉ።
ይህን ጉዳይ ይዘን ካይሮ የሚገኘዉን የ «UNHCR» ጽ/ቤት ለማነጋገር ያደረግነዉ ጥረት አልተሳካም። ሆኖም ጄኔቫ ስዊዘርላንድ የሚገኘዉ የድርጅቱ ዋና ጽ/ቤት ቃል አቀባይ አርያን ሪመሪ ጉዳዩን እንደሰሙና እንዳሳዘናቸዉ ተናግረዋል።
«በዚህ ጉዳይ ላይ መናገር የምችለዉ «UNHCR » በካይሮ በሚገኘዉ ጽ/ቤቱ ፊት ለፊት ትናንት በተከሰተዉ አጋጣሚ በጣም ማዘኑን ነዉ። ሦስት ኦሮሞ ተገን ጠያቂዎች ራሳቸዉን በእሳት አቃጥለዋል። ካይሮ የሚገኘዉ የ«UNHCR» የደሕንነት ጥበቃ አባላት እሳቱን ለማጥፋት ጥረት አድርገዋል። የተጎዱት የሕክምና ርዳታ እንዲያገኙ ያመቻቹ ሲሆን፤ ከመካከላቸዉ አንዱንም ወደሀኪም ቤት ወስደዋል። በቃጠሎዉ ለሞት የሚያሰጋ ጉዳት አልደረሰም።»
አርያን ሪመሪ ጥገኝነት ፈላጊዎቹ ያጋጠማቸዉን ችግር ለማቅለልም ድርጅታቸዉ እየሠራ እንደሆነም ይናገራሉ።
«UNHCR» ከኦሮሞ መሪዎች ጋር በርካታ ስብሰባዎችን አድርጓል። መፍትሄ ለማግኘትም ከነሱ ጋር በትብብር እየሠራን ነዉ።»
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሰ