ማህበሩ በአቅም ውስንነት ያቀዳቸውም ሥራዎች መከወን ተቸግሯል
ዓርብ፣ ሐምሌ 29 2008
በ2004 ዓ.ም ከባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ በህግ የተመረቁ ተማሪዎች የተጠነሰሰው የኢትዮጵያ ወጣት የህግ ባለሙያዎች ማህበር ዛሬ ከ500 በላይ አባላት አሉት። ለማህበሩ አባልነት ቢያንስ የዲፕሎማ ሰርተፍኬት ያስፈልጋል። አቃብያነ-ህግ፤ዳኞች እንዲሁም በመንግስት እና መንግስታዊ ባልሆኑ ተቋማት በህግ ባለሙያነት የሚያገለግሉ ወጣት አባላት አሉት። ማህበሩ ሰባት የሥራ አስፈጻሚዎች እንዲሁም ሶስት አባላት ያሉት ቦርድ አለው።
በኢትዮጵያ ወጣት የህግ ባለሙያዎች ማህበር ድረ-ገጽ የህግ ሙያ እንዲዳብር፤የህግ-የበላይነት እና የሰብዓዊ መብት እንዲከበር አስተዋፅዖ ማድረግ ተልዕኮዉ መሆናቸው ሰፍሯል። የኢትዮጵያ ወጣት የህግ ባለሙያዎች ከፍ ያለ ብቃት ያላቸው ሆኖ የማየት ርዕይ ማህበሩ ሰንቋል። የኢትዮጵያ ወጣት የህግ ባለሙያዎች ማህበር የህግ ድጋፍ ለሚሹ ዜጎች የማማከር አገልግሎት እንደሚሰጥ ወንድይፍራው ግዛቸው ተናግሯል።
በኢትዮጵያ የፍትህ ተቋማት ውስጥ በዳኝነት፤በአቃቤ-ህግነት የሚያገለግሉ ባለሙያዎች አብዛኞቹ ወጣቶች ናቸው የሚለው ወንድይፍራው የማህበራቸው ስራዎች በቀጥታ እነዚህን ወጣት ባለሙያዎች ተጠቃሚ እንደሚያደርጉ ያምናል። ይሁንና ስራቸውን ለመከወን የአቅም ውስንነት አለባቸው።
የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች «በ2009 ዓ.ም የወጣው የበጎ አድራጎት ድርጅቶች እና ማህበራት አዋጅ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች በሰብዓዊ መብቶች ዙሪያ የመስራት አቅማቸውን በእጅጉ ይገድባል» ሲሉ ይተቻሉ።
እሸቴ በቀለ
ነጋሽ መሀመድ