1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች እርስ በርስ ይተማመናሉ? ሕዝቡስ?

እሑድ፣ መጋቢት 2 2010

የተቃውሞው ልክ የኢሕአዴግ አባል ፓርቲዎች በሚያስተዳድሯቸው ክልሎች እኩል አይደለም። የታሰሩ፣ የሞቱ ሰዎች ቁጥርም እንደዚያው። አባል ፓርቲዎቹ ተቃውሞዎቹን፣ ትችቶች እና ጥያቄዎቹን በአጠቃላይ የፖለቲካ አለመረጋጋቱን የሚረዱበት፣ የሚተነትኑበት እና የመፍትሔ ሐሳብ የሚፈልጉበት መንገድ በኢሕአዴግ ዘንድ ምን አይነት ልዩነት ይፈጥራል?

https://p.dw.com/p/2u7dy
Äthiopien vor der Wahl EPRDF Anhänger in Addis Abeba
ምስል Getty Images/AFP/Z. Abubeker

ውይይት፥ የኢሕዴግ የውስጥ ፖለቲካና እምነት

በውስጡ የበረታ ክፍፍል ገጥሞታል የሚባለው ኢሕአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ለስብሰባ ተቀምጧል። ግንባሩ በአባል ፓርቲዎቹ መካከል ልዩነት መኖሩን ቢያረጋግጥም ምክንያቶቹን ግን በይፋ ከመግለፅ ተቆጥቧል። የኢሕአዴግ ተቺዎች እና የፖለቲካ ተንታኞች ክፍፍሉ በተራማጅ ኃይሎች እና ነባሩን ሁኔታ ማስቀጠል በሚፈልጉ መካከል ሳይሆን አይቀርም የሚል እምነት አላቸው። ግንባሩ አሁን ባለው ቁመናና በአባል ፓርቲዎቹ መካከል ባለው ልዩነት ምክንያት አገሪቱ የገባችበትን ውጥንቅጥ መፍታት ስለመቻሉም ጥርጣሬ አላቸው። "የኢሕአዴግ የውስጥ ቅራኔ አፈታት ዴሞክራሲያዊ አይደለም" የሚሉት ተንታኞች በህዝቡ ዘንድ የነበረውን ቅቡልነት ማጣቱንም ይናገራሉ። 

ልዩነቱ ቢፈጠር እንኳ ተፈጥሯዊ ነው። ግንባሩን ያበረታዋል የሚሉ ሰዎች አሉ። ለ27 አመታት ገደማ አገሪቱን ያስተዳደረውን ግንባር የውስጥ ልዩነት ያዳክመዋል ወይስ ያበረታዋል? የዜጎችን ሰላም እና ደሕንነት ማረጋገጥ፣ ተቋማትን መጠበቅ የመንግሥት ኃላፊነት ነው። መንግሥታት ለሚታወቁ ሥጋቶች መትሔ የመሻት ለማይታወቁት አስቀድሞ መዘጋጀት ይጠበቅባቸዋል። ኢሕአዴግ ችግሮች በገጠሙት ቁጥር በተደጋጋሚ ራሴን ፈትሻለሁ፣ ለአገራዊ ችግሮች መፍትሔ አበጅቻለሁ ሲል ይደመጣል። ነገር ግን ተቃውሞው ሲበረታ ይታያል። ኢሕአዴግ በሚመራው መንግሥት እና በሕዝብ ዘንድ በተለይ በከተሞች እና ወረዳዎች አደባባይ በወጡ ወጣቶች ዘንድ ያለው መተማመን ምን አይነት ነው?የዛሬው የእንወያይ መሰናዶ የኢሕአዴግ የውስጥ ሽኩቻ እና ግንባሩ የሚመራው መንግሥት በሕዝብ ዘንድ ያለው ተቀባይነት ላይ ያተኩራል። 

እሸቴ በቀለ

ልደት አበበ