የአድዋ ድል 120ኛ ዓመት መታሰቢያ
ረቡዕ፣ የካቲት 23 2008ኣየአድዋ ድል 120ኛ መታሠቢያ በዓል ካለፈው ዓመት ለየት ባለ መልኩ ዘንድሮ በአዲስ አበባ ከተማ እና በመላው ሀገሪቱ በደማቅ ሁኔታ መከበሩ ተገለጠ።
በመዲናዪቱ አዲስ አበባ በዳግማዊ ምንሊክ ሀውልት ስር ዛሬ በተከናወነው የመታሠቢያ ሥነ ሥርዓት በዓል ላይ አባት እና እናት አርበኞች፣ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ አባ ዱላ ገመዳ፣ የመንግሥት ባለሥልጣናት፤ ነዋሪዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። የውጭ ሃገራት ዲፕሎማቶች እና የአፍሪቃ ኅብረት እንግዶችም እንዲመጡ ግብዣ መደረጉን አባት አርበኞች ተናግረዋል።
ባለፈው ዓመት የአበባ ማስቀመጥ ሥነ-ሥርዓት ብቻ ይከናወን እንደነበር የገለጡት የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች ማኅበር ፕሬዚዳንት ልጅ ዳንኤል ጆቴ መሥፍን የዘንድሮ በዓልን ለየት የሚያደርገው ነገር አለ ብለዋል፦ «ከውጭ ጉዳይ ሚንሥቴር በደረሰን ወረቀት ዜና የጣሊያኑ ፕሬዚዳንት ኢትዮጵያ በሚመጣው 13 ቀን ውስጥ እንደሚመጣ እና በድል ሀውልታችን ላይ አበባ እንደሚያስቀምጥ ስለተነገረን ለእኛ ትልቅ ደስታ እንደተሰማን ነው።»
ዘንድሮ በተከናወነው የአድዋ ድል 120ኛ ዓመት መታሠቢያ ሥነ ሥርዓት ለአባት አርበኞች የተሻለ ቦታ እንደተሰጣቸው የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች ማኅበር ፕሬዚዳንት ልጅ ዳንኤል ጆቴ መሥፍን ተናግረዋል። ወኪላችን ጌታቸዉ ተድላ ኃይለጊዮርጊስ ከአዲስ አበባ በላከልን ዘገባም በመንግሥት በኩል ቀድሞ ከሚከበረዉ በላቀ ደረጃ ትኩረት እንደተሰጠዉ አመልክቷል። በዛሬዉ ክብረ በዓል ላይም በአራዳ ጊዮርጊስ ታሪክ ተረካቢ የሚሆኑት ወጣት ተማሪዎች ትርኢት አቅርበዋል።
ጌታቸዉ ተድላ ኃይለጊዮርጊስ/ ማንተጋፍቶት ስለሺ
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ