የአዲስ አበባ ደረቅ ቆሻሻ ያስነሳው ንትርክ
ሰኞ፣ ሐምሌ 18 2008የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳደር «ሰንዳፋ ሳኒተሪ ላንድ ፊል» በሚል ባስገነባው የደረቅ ቆሻሻ ማጠራቀሚያ ላለፉት ሰባት ወራት ሲጠቀምበት እንደቆየ የአገር ዉስጥ መገናኛ ብዙኃን አመልክተዋል። ይሁንና፣ የዚሁ የደረቅ ቆሻሻ ማጠራቀምያ ጉዳይ ከነዋሪዎች ቁጣ ካስነሳ በኋላ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና የኦሮሚያ ክልል ውይይት ቢያካሂዱም፣ ስምምነት ላይ አለመድረሳቸው በመጨረሻም አዲስ አባባ ከተማ መስተዳድር ሌለ አማራጭ ቦታ ለመፈልግ እንደተገደደ ነው የተሰማው።
ሁለቱም መስተዳደሮች ሳይወያዩና ሳይስማሙ እንዴት ወደ ደረቅ ቆሻሻ ማጠራቀምያ ግንባታዉም ሆነ አጠቃቀም ውስጥ እንደተገባ ለማወቅ ሁለቱንም የመንግስት አካላት ለማናገር ያደረግነዉ ሙከራ አልተሳካልንም። ይሁን እንጅ፣ በግል ተደራጅተው ካለፉት አምስት ዓመታት ወዲህ በደረቅ ቆሻሻ ማንሳት አገልግሎት ላይ የተሰማሩትን የ«ሰርካለም እና አስቻለዉ የደረቅ ቆሻሻ ማንሳት ማህበር» ስራ አስካያጅ አቶ አስቻለው ባዬ ጉዳዩን እንዴት እንደሚመለከቱት እና የተወሰደዉ ርምጃ ምን አይነት ተፅኖ እንዳለዉ አነጋግራቸዉ ነበር።
የአዲስ አበባ መስተዳደር በሰንዳፋ ነዋሪዎች መሃል የተፈጠረዉን ችግር ለኅብረተሰቡም ሆነ ለግል ደረቅ ቆሻሻ አገልግሎት ለሚሰጡት ግልጽ አላደረገም የሚሉት በዚህ ስራ በግል የተሰማሩት አቶ አረጋ አብራሃ በስራችን ላይ ተፅኖ አሳድረዋል ይላሉ።
አቶ አስቻለዉ በሁለቱ መስተዳድር መካከል በተፈጠረው ንትርክ እየገጠማቸው ያለውን ችግር ለማስወገድ ይቻል ዘንድ ቀጣዩን ሀሳብ አቅርበዋል።
አንዳንድ የድረ ገፃችን ተከታታዮች ይህ የቆሻሻ ማጠራቀምያ ቦታ ሲገነባ የሚመለከታቸዉ አካላት የት ነበሩ ሲሉ ? ሌሎች ደግሞ ይህ መጀመርያ ለኢንዱስትሪ ዞን ታቅዶ ነበር የተባለውን መሬት ለአዲስ አበባ ቆሻሻ መጣያ ማድረግ «መስተዳድሩ ለአካባቢው ሕዝብ ያለውን ንቀት በግልጽ ያሳየበት ውሳኔ» ነው ሲሉ ተችተዋል። በአዲስ አበባ የሚመነጭ ቆሻሻ እዛዉ አድስ አበባ ዉስጥ ቦታ ተፈልጎለት እንድወገድ መድረግ ይገባዋል ሲሉም አስተያየታችዉን ሰንዝረዋል።
መርጋ ዮናስ
አረያም ተክሌ