1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአንካራዉ መንግሥት በጀርመን ቱርኮችን ይሰልላል

ማክሰኞ፣ መጋቢት 19 2009

የቱርክ የስለላ ድርጅት ቱርካዊዉን የሃይማኖት መሪ ፈቱላህ ጉለንን ይደግፋሉ ያላቸዉን በጀርመን ሀገር የሚኖሩ የቱርክ ዜጎች እንደሚሰልል የጀርመን የብዙኃን መገናኛዎች ዘገቡ። «ዚውድዶይቸ» የተባለው የጀርመን ዕለታዊ ጋዜጣ ከሌሎች የሃገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ጋር በጋራ ያካሄደው የምርመራ ውጤት እንደሚያመለክተዉ የጉለን ተከታዮች ስም ዝርዝር ተይዞአል።

https://p.dw.com/p/2aAi8
Symbolbild Deutschland - Türkei
ምስል picture-alliance/dpa/P. Zinken

የቱርክ የስለላ ድርጅት ቱርካዊዉን የሃይማኖት መሪ ፈቱላህ ጉለንን ይደግፋሉ ያላቸዉን በጀርመን ሀገር የሚኖሩ የቱርክ ዜጎች እንደሚሰልል የጀርመን የብዙኃን መገናኛዎች ዘገቡ። «ዚውድዶይቸ» የተባለው የጀርመን ዕለታዊ ጋዜጣ ከሌሎች የሃገሩ መገናኛ ብዙኃን ጋር በጋራ ያካሄደውን ምርመራ ውጤት በመጥቀስ እንደገለጸው፣ በምህፃሩ «ሚት» በሚል መጠሪያ የሚታወቀው የቱርክ የስለላ ድርጅት የጉለን ተከታዮች የተባሉ የአንድ መቶ የቱርክ ዜጎች ስም አለዉ። የስለላ ድርጅቱ ከያዛቸዉ 300 የስም ዝርዝሮች በተጨማሪ 200 የጉለን መርህ አራማጅ ማኅበራት፤ ትምህርት ቤቶችንና ሌሎች ተቋማትም ይገኙበታል። የስም ዝርዝሩ የተገኘዉ፤ በመኖርያ አድራሻ፤ በተንቀሳቃሽና በመኖርያ ቤት የስልክ ቁጥር ማዉጫ መዘርዝር ላይ ጭምር ነዉ።
የአረንጓዴ ፓርቲ አባልና የጀርመን ምክር ቤት ም/ አፈ-ጉባዔ ሊቀመንበር ክላውድያ ሮት፤ ለዶቼ ቬለ በሰጡት ቃለ ምልልስ የቱርክ ፕሬዚዳንት ርምጃ ተቀባይነት የሌለዉ ነዉ ብለዋል።
«ባለፈዉ ሳምንት በዚህ ጉዳይ ላይ ፓርላማ ዉስጥ ተነጋግረናል ፤ ዳግም በዚሁ ጉዳይ ላይ እንነጋገራለን ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።  እዚህ ጀርመን ውስጥ  በሰላምና በነፃነት ነው የምንኖረው። ሰዎች መሰለላቸዉ ፤ በስጋት መኖራቸው  ፍርሃት መዋጣቸዉ በፍፁም ተቀባይነት የሌለው ነገር ነዉ።  እነዚህ ሰዎች ወደ ቱርክ ከተመለሱ ሊደርስባቸው ስለሚችለው ጥግር ማሳሰቢያ ሊሰጣቸው ይገባል።  ይህ ተቀባይነት የሌለዉ ርምጃ ነዉ። መንግሥት በቱርክ የሚታየው ውዝግብ፣ ክፍፍሉ፣ ልዩነቱ እና የኃይሉ ተግባር የሚባባስበት ሂደት ወደ ሃገራችን፣ ወደኛ ህብረተሰብ  ሊመጣ እንደማይገባው ግልጽ ያደርጋል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።  የመናገር ነፃነት ፤የፕሬስ ነጻነት እንዲኖረን እንፈልጋለን፤ እና ማንም ሰው ፣ ኤርዶኻን ጠላት አድርገው ስላዩት ብቻ፣ እንደ አሸባሪ እንዲቆጠር አንፈልግም። »
በጎርጎረሳዊ 2016 ዓ,ም ሐምሌ ወር ለተካሄደዉ የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ በዩኤስ አሜሪካ በስደት የሚኖሩትን ቱርካዊዉን ሃይማኖተኛ መሪ ፈቱላህ ጉለንን ተጠያቂ የሚያደርገዉ የቱርክ መንግስት የጉለንን ተከታዮች «አሸባሪ» ስል መፈረጁም ይታወቃል።      
 

 

አዜብ ታደሰ

አርያም ተክሌ