የአበረታች ንጥር ነገር ምርመራ እና ኢትዮጵያ
ሰኞ፣ ሚያዝያ 3 2008ባለፈዉ ሳምንት ደግሞ ኢትዮጵያ 200 የሚገመቱ አትሌቶች ላይ ምርመራ እንድታካሂድ፤ ይህን ባታደርግ WADA ርምጃ እንደሚወስድ ከዛም አልፎ IAAF የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሸንን ከዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ዉድድሮች እንደሚያግድ ማስጠንቀቅያ ተሰጥቷል።
ይህ ከአትሌቶች ጋር የተያያዘዉ አበራታች ንጥር ነገር ቅሌት በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ላይ ሊኖረዉ የሚችለዉን ተፅዕኖ ለመቋቋም የኢትዮጵያ የወጣቶች፣ ስፖርት እና ባህል ሚኒስቴር ሁለት ጉዳዮች ላይ አተኮሮ እየሠራ መሆኑን ሚኒስትሩ አቶ ሬዱዋን ሁሴን ይናገራሉ። እንደ እሳቸዉ ገለፃ አንዱ <<በጣም ሰፋፊ የማስተማር ሥራዎች በህብረተሰቡ መሃል መሥራት>> እና ሁለተኛዉ የፀረ አበራታች ንጥር ነገር ፅሕፈት ቤት ማቋቋም እና ለምርመራዉ በቂ የቴክኒክ እና የገንዘብ አቅም እንዲኖረዉ ማድረግ ነዉ። ከ120 እስከ 200 አትሌቶችን ለመመርመር ኮታ እንደተሰጣቸዉ የገለጹት አቶ ሬዱዋን ባለሙያዎችን መድቦ ምርመራዉን ለማካሄድ መዘጋጀቱን ለዶቼ ቬለ አስረድተዋል።
የቅጣቱን መጠንም እንደተወሰደዉ የመድኃኒቱ ክብደትና ቅለት፣ መድኃኒቱ የተወሰደበት ሁኔታ እና ምክንያት ላይ እንደሚወሰንም አቶ ሬዱዋን ገልጸዋል። ከዚያም ከሁለት ዓመት ጀምሮ እስከ እድሜ ልክ የመታገድ ቅጣት ሊኖር እንደሚችልም አብራርተዋል። እስካሁን የተቀጡ አትሌቶች በቅጣቱ ምክንያት ኪሳራ ዉስጥ እንደገቡ አቶ ሬዱዋን ይናገራሉ።
ይህ የፀረ አበራታች ንጥር ነገር ቅሌት እየበዛ ከሄደ አትሌቶች በራሳቸዉ ጥረት ያገኙትን ገፅታ እና አገሪቱም በአትሌትክስ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላት ተቀባይነት ላይ ጠባሳ ሊያሳርፍ እንደሚችልም አቶ ሬዱዋን ገልፀዋል። ይህን ጉዳይ አስመልክቶ በዶቼ ቬሌ የፌስ ቡክ ገፅ ላይ ከአድማጮች ጋር በተደረገዉ ዉይይት አብዘኞች ሚኒስቴር መሥርያ ቤቱ እና የሚመለከተዉ አካል አገሪቱ በዚህ ረገድ ያላትን ገፅታ ለማስተካከል ብዙ መሥራት እንዳለባቸዉ ጠቁመዋል።
መርጋ ዮናስ
ሸዋዬ ለገሠ