1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅና የድፒሎማትክ ማህበረሰቡ ምላሽ

Merga Yonas Bula
ረቡዕ፣ የካቲት 14 2010

በኢትዮጵያ ዉስጥ ያለዉን የፖለትካ አለመረጋጋትን ተከትሎ ባለፈዉ ሳምንት መንግስት ለሁለተኛ ግዜ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አውጀዋል።

https://p.dw.com/p/2t6K9
Dr Workneh Gebeyehu äthiopischer Außenminister 23.01.2018
ምስል Getachew Tedla, HG

የአዋጁ አስፈላጊነት ከዜጎች አልፎ በአለም ዓቀፉ  ማህበረሰብ ላይም ጥያቄ መፍጠሩን ዘገባዎች ያመለክታሉ። በትላንትናዉ እለትም የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ወርቅነህ ገበየሁ ስለ አዋጅ አስፈላጊነት መቀመጫቸዉን አዲስ አበባ ላደረጉት የዉጭ ድፒሎማቶች ገለፃ አድርገዋል። በገለፃቸዉም የፀጥታ ስጋት እንደለሌ ሆኖም መንግሥት አዋጁን የደነገገው «በመደበኛ የሕግ አስከባሪ አካላት አማካኝነት ያለውን አለመረጋጋት መቆጣጠር ስላልተቻለ» ነው ሲሉ ተናግረዋል። 
የሕግ ባለሙያና ጠበቃ አቶ ተማም አባቡልጉ ሚንስትሩ የፀጥታ ስጋት የለም ማለታቸው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሲደነገግ በሀገሪቱ አለመረጋጋት ስላለ ነዉ ከተባለው ጋር  የሚጣረስ ነዉ ይላሉ።

አዋጁ ስለ ታወጀበት ምክንያት ዶክተር ወርቅነህ ስለ ሰጡት ገለፃ የዶይቼ ቬሌ ተከታታዮች አስተያየቶቻቸዉን ገልፀዋል። ወርቁ ፋራዳ የሚል የፌስቡክ ስም የያዘዉ ግለሰብ ሚንስትሩ ያሉትን በመደገፍ «አገሪቱ ለይ ያለው የፖለቲካ ቀውስ አስቸጋሪ ከሆነ አዋጁ ትክክል ነው» ካለ በኋላ «ስርዓተ መንግስቱ ይሆናል ብሎ ያመነበትን አዋጅ አንደ ህገ መንግስቱ የማወጅ መብት አለው፣ ጣጣ የለውም» ስል አስተያየቱን አስፍረዋል። ነብዩ ንጉሴ በተቃራኒ ሚንስትሩ ያሉት እርስ በርሱ ይጋጫል፤ ምክንያቱም በአንድ መልክ የፀጥታ ችግር የለም እየተባለ «አለመረጋጋቱን በመደበኛው የሕግ አስከባሪ መቆጣጠር ስላልተቻለ ነው በማለታቸዉ ነዉ ይላል። አስተያየቶቻቸዉን በድምጽ የላኩልንም አሉ።

ከአስተያየት ሰጭዎቹ መካከል የኢትዮጵያ መንግስት የወሰደዉ ርምጃ ከፍርሃት የመነጨ ነዉ የሚሉም አሉ። የሕግ ባለሙያዉ አቶ ተማም አባቡልጎም ተመሳሳይ አስተያየት ሰጥተውናል።

ከዚህ ቀደም ባልታየ መልኩ መቀመጫቸዉን በአዲስ አበባ ያደረጉት ኤምባሲዎችን ጨምሮ የተለያዩ አገራት የዉጭ ጉዳይ ቢሮዎች አዋጁን በተመለከተ የተሰማቸዉን ስጋት ኢየገለፁ ነው። ለምሳሌ የጀርመን የዉጭ ጉዳይ ቢሮ ትላንት ባወጣዉ መግለጫ አዋጁ በሲቭል መብቶች ላይ ተፅእኖ እንዳለዉ ገልፀዋል። የዩናይትድ ስቴትስ ኤምባሲም ቅዳሜ ባወጣዉ መግለጫ የኢትዮጵያ መንግስት የወሰደዉ ዉሳኔ መሰረታዊ መብቶችን፤ በተለይም ሃሳብን በነፃ የመግለፅና የመሰብሰብ መብቶችን ስለሚገድብ አጥብቆ እንደሚቃወም ገልፀዋል። የኢትዮጵያ መንግስት በአሜሪካ ኤምባስ መግለጫ ደስተኛ ስላልሆነ በኢትዮጵያ የአሜሪካን አምባሳደር ማብራሪያ እንዲሰጡ መጠየቁን ሪፖተር ጋዜጣ ዘግቧል።

ሙሉ ዘገባዉን ለማዳመጥ ከላይ ያለዉን ኡዲዎ ይጫኑ።

መርጋ ዮናስ

ኂሩት መለሰ