የትራምፕ ድል፤ድንጋጤና አስተያየት
ረቡዕ፣ ጥቅምት 30 2009
ከሁለት ወር በፊት ጋጤጠኛዉ ዩናይትድ ስቴትሱን ፕሬዝደንት ባራክ ኦቦማን ጠየቃቸዉ።ዶናልድ ትራምፕ ይመረጣሉ ብለዉ ያስባሉ» ዓይነት ብለዉ።«የምርጫ በፊት አስተያየት እዉነት ቢሆን ኖሮ» መለሱ ፕሬዝደንቱ፤ «እኔ አልመረጥም ነበር» እያሉ።እና አሜሪካዉያን መረጡ።አንዲት ጀርመናዊት ጋዜጠኛ ዛሬ ጧት እንዳለችዉ የአብዛኛዉ ዓለም ፖለቲከኞች ደነገጡ።አሜሪካዉያን አሜሪካ ዉስጥ የማይሆን የለም የሚል ፈልጥ አላቸዉ።ለብዙዎች የማይሆን የመሰለዉ ሆነ። ዶናልድ ጆን ትራምፕ የትልቅ፤ ሐብታም፤ልዕለ ሐያሊቱ ሐገር ፕሬዝደንት ሆነዉ ተመረጡ።የምርጫዉ ሒደት፤ የድሕረ ምርጫዉ ዕዉነት፤ የዓለም አስተያየት የዛሬዉ ዜና መፅሔታችን ርዕስ ነዉ።ተራ፤ በተራ እንመለከተዋለን።
ከዋሽግተን እንጀምር።ቢሊየነሩ ቱጃር ዶናልድ ትራምፕ ተቀናቃኛቸዉን ወይዘሮ ሒላሪ ክሊንተንን በከፍተኛ ልዩነት ነዉ ያሸነፏቸዉ።በአሜሪካኖች የፕሬዝደንታዊ ምርጫ ደንብ መሠረት Electorale Vote ከሚባለዉ ድምፅ ትራምፕ 289ኙን ሲያገኙ፤ ሒላሪ ክሊንተን 218 ብቻ ነዉ ያገኙት።ለምን ደግሞስ እንዴት?።የዋሽግተን ዲሲዉ ወኪላችን መክብብ ሸዋ የድምፅ አሰጣጡን ሒደትና ዉጤት የሚቃኝ ዘገባ አለዉ።
የቅድመ ምርጫ አስተያየት፤ ትንበያ፤ የፖለቲካ ተንታኞች መላ ምት እርግጥ ቢሆን ኖሮ ዛሬ የድል ጮቤ ረጋጭ-አስረጋጭዋ ሒላሪ ክሊንተን በሆኑ ነበር።የፖለቲካ ዲፕሎማሲዉ ዕዉቀት፤ሥራ እና ልምድ ቢያስመርጥ ኖሮ ትራምፕ፤ እንደ ተማሪ፤ እንደ ቀዳማዊት እመቤት፤ እንደ ሴናተር፤ እንደ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ፖለቲካ-ዲፕሎማሲን ጥርሳቸዉን የነቀበሉበትን ክሊንተን ጨርሶ ባልተፎካከሩ ነበር።ከዕዉቅ ፖለቲከኞች፤ ከሚንስትር መሪዎች መዛመድ፤መወዳጀት፤ መቀራረብ ለመመረጥ ቢረዳ ኖሮ ትራምፕ፤ ክሊንተን በቆሙበት ባልተገኙ ነበር።አንዱም አልሆነም።ትራምፕ አሸነፉ።የአዲስ አበባዉ ወኪላችን ዮሐንስ ገብረ እግዚአብሔር ያነጋገራቸዉ ኢትዮጵያዊዉ አስተያየት ሰጪዎች ከምርጫዉ ዉጤት ይልቅ ሒደቱ አስደስቷቸዋል።አንዱ «አቦስቶ» አሉት።ቋንቋዉ ባይገባንም መልዕክቱ «ድንቅ» የሚል ነዉ ብለን እንገምት።
የፌስ ቡክ ዉይይታችንም ሌላ ርዕስ አልነበረዉም።የአሜሪካኖች ምርጫ አንጂ።ተመራጩ ፕሬዝደንት የዉጪ በተለይም አፍሪቃና የኢትዮጵያን የሚመለከት መርሐቸዉ ከተሰናባቹ ፕሬዝደንት መርሕ በምን ይለያል የሚል ይዘት ያለዉ ሐሳብ ቀርበቦት ነበር።የዕለቱን ዉይይት የመራዉ መርጋ ዮናስን አነጋግሬዋለሁ።
ያልታሰበዉ የዶናልድ ትራምፕ ድል አዉሮጳንና ጀርመንን ክፉኛ ማስደንገጡን የዶቼ ቬለዉ አሌክሳንደር ኩዳሼቭ የጻፈዉ ሃተታ ያመለክታል። ሁኔታዉ ከመደናገጥ አልፎ ግራ መጋባትን እና ይህ እንዴት ይሆናል የሚል ጥያቄም ማስከተሉንም ይዘረዝራል። የበርሊኑ ዘጋቢያችን ይልማ ኃይለ ሚካኤል ሃተታዉን እንደሚከተለዉ አጠናቅሮታል።
መክብብ ሸዋ
ዮሐንስ ገብረእግዚአብሔር
መርጋ ዮናስ
ይልማ ሐይለ ሚካኤል
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሰ