የተለያዩ ወረርሽኞች መከሰት
ማክሰኞ፣ መጋቢት 27 2008የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ከሳምንታት በፊት የአጣዳፊ ተቅማጥ እና ተዉከትን ለማስከተል ምክንያቶች የሚባሉትን በመዘርዘር ሊደረጉ ስለሚገባቸዉ ጥንቃቄዎች መግለጫ ማዉጣቱን የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ተቋም ድረገጽ ያመለክታል። በሽታዉ እስካሁን በሰዉ ሕይወት ላይ ምን ያህል ጉዳት እንዳደረሰ ግን አልተነገረም። ኢትዮጵያ ዉስጥ በአንዳንድ አካባቢዎችም ማጅራት ገትር በመባል የሚታወቀዉ በሽታም እንዲሁ በመከሰቱ ተሰምቷል።
ኢትዮጵያ ዉስጥ የአጣዳፊ ተቅማጥ እና ተዉከት በሚል ለሚገለጸዉ ሕመም መነሻዉ የግል እና የአካባቢ ንጽሕና ጉድለት ላይ በቂ ንጹሕ የመጠጥ ዉኃ አቅርቦት አለመኖር መሆኑን ያመለከተዉ የጤና ጥበቃ መግለጫ፤ በበሽታዉ የተያዘ ሰዉ ስለሚኖሩት ምልክቶች ይዘረዝራል፤ ምልክቶቹ አጣዳፊ መጠነ ብዙ ዉኃማ ተቅማጥ፣ ትዉከት እና ቁርጥማት፣ የዓይን መሰርጎድ፤ የአፍና የምላስ መድረቅ፣ እንባ አልባ መሆን የሽንት መጠን መቀነስ፤ የቆዳ መድረቅ እና መሸብሸብ፤ እንዲሁም የሰዉነት ድርቀት ናቸዉ። ስነዚህ ምልክቶች የታዩበት ሰዉ በትክክል በሽታ ተይዟል የሚለዉን መገመት ቢቻልም በምርመራ ታግዞ ሲረጋገጥ ታማሚዉ ባስቸኳይ ህክምና እንዲያገኝ ማድረግ ያስፈልጋል። ታማሚዉ ወደላይም ሆነ ወደታች የሚለዉ በመበርከቱ ከሰዉነቱ በርካታ ፈሳሽ ስለሚወጣ ተገቢዉን የህክምና ርዳታ ካላገኘ ሕይወት እስከማሳጣት ሊያደርስ የሚችል በሽታ መሆኑም ተገልጿል። ከአድማጭ የደረሰን መረጃ ደግሞ ምንነቱ ያልተለየ ለሞት የሚያበቃ በሽታም ጉዳት ማድረሱን ይገልጻል። ዝርዝሩን ከድምጽ ዘገባዉ ያድምጡ
ሸዋዬ ለገሠ
አዜብ ታደሰ