1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሳዑዲ አረቢያና የኢራን እንኪያ ሰላንቲያ

ነጋሽ መሐመድ
ሰኞ፣ ሚያዝያ 30 2009

የሳዑዲ አረቢያዉ ምክትል አልጋወራሽና መከላከያ ሚንስትር መሐመድ ቢን ሠልማን ቴሕራኖችን ለመወንጀል የትራምፕን የማበረታቺያ ጉብኝት አልጠበቁም። «የኢራን ዋና ኢላማ እንደሆንን እናዉቃለን» አሉ፤ የ32 ዓመቱ ጎርምሳ በቀደም«ግን ጦርነቱ ሳዑዲ አረቢያ ዉስጥ እስኪደረግ አንጠብቅም። ኢራን ዉስጥ እንዲሆን እንሰራለን እንጂ።»

https://p.dw.com/p/2cd1p
Saudi-Arabien Militärparade in Mekka
ምስል picture-alliance/dpa/K. El Fiqi

የሳዑዲ አረቢያና የኢራን እንኪያ ሰላንቲያ

ኢራን እና ዩናይትድ ስቴትስ በኑክሌር መርሐ-ግብር ሰበብ 12 ዓመታት ገጥመዉት የነበረዉን ዉዝግብ፤  ግጭት በሰላም መፍታታቸዉን ከተቃወሙት ሁለት መንግሥታት አንዱ የሳዑዲ አረቢያ ነዉ። በኢራን ይደገፋል የሚባለዉን የሶሪያ መንግሥት ለማስወገድ ቢሊዮነ-ቢሊዮናት ዶላር በማፍሰስ ሳዑዲ አረቢያን የቀደመ የለም። በቴሕራን ይረዳሉ የሚባሉትን የየመን ሁቲ አማፂን ለመደምሰስ ሪያዶች አረብ-አፍቃሪቃዎችን መርተዉ የመን ላይ የለኮሱት እሳት ደሐዊቱን ዓረብ ሐገር እያወደመ፤ ሕዝቧን እየፈጀ፤ ወላፈኑ ኤርትራም ተሻገረ። የሪያድ እና የቴሕራን የሳምንቱ ማብቂያ ዛቻ ደግሞ ከእስካሁኑም የባሰ ጥፋት እንዳያስከትል አስግቷል። 
                                    
ኢትዮጵያዊዉ የፖለቲካ ተንታኝ ዩሱፍ ያሲን «ቁማር» ይሉታል፤ የሪያድ-ቴሕራኖችን ቀጥታ-እና ተዘዋዋሪ ዉጊያ። ቁማሩ ኢራቅን የአሸባሪዎች መናኸሪያ አድርጓታል። ሊቢያን የየጎጥ ነፍጠኞች መዋጊያ አድርጓታል።ሶሪያን እያጠፋ፤ የመንን እያወደመ ነዉ። ሪያድ-ቴሕራኖች ቁማርተኞቹ ከሆኑ፤ ዋና አጋፋሪዋ ዩናይትድ ስቴትስ መሆኗ አለጠያየቀም።የሪያዱ ወኪላችን ስለሺ ሽብሩ ይሕንኑ ያረጋግጥልናል።
                                             
የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ የመጀመሪያዉን የዉጪ ሐገር ጉብኝታቸዉን ከሳዑዲ አረቢያ ጀምረዉ፤ በእስራኤል ቀጥለዉ፤ ቫቲካን ላይ ያሰልሳሉ ተብሏል። ሳዑዲ አረቢያን ያስቀደሙበት ምክንያት መቼም ዑሙራ ሊያደርጉ ነዉ ሊባል አይችልም። የተሰጠዉ ሰበብ ግን የሰዎስቱን ነባር ኃይማኖታዊ ሥፍራዎች አስቀድሞ መጎብኘት የሚል ነዉ። ለፖለቲካ ተንታኞች  አሳማኙ ምክንያት ግን የጦር መሳሪያ ሽያጭ-አንድ፤ ሳዑዲ አረቢያንና እስራኤሎችን ማበረታት-ሁለት፤ የካቶሊኮችን ድጋፍ መሻት ሰዎት ናቸዉ።
የሳዑዲ አረቢያዉ ምክትል አልጋወራሽና መከላከያ ሚንስትር መሐመድ ቢን ሠልማን ቴሕራኖችን ለመወንጀል የትራምፕን የማበረታቺያ ጉብኝት አልጠበቁም። «የኢራን ዋና ኢላማ እንደሆንን እናዉቃለን» አሉ፤ የ32 ዓመቱ ጎርምሳ በቀደም«ግን ጦርነቱ ሳዑዲ አረቢያ ዉስጥ እስኪደረግ አንጠብቅም። ኢራን ዉስጥ እንዲሆን እንሰራለን እንጂ።»
                       
የኢራኑ መከላከያ ሚንስትር ጄኔራል ሁሴይን ዴግሐን አፀፋም ቀላል አልነበረም። «ሳዑዲዎች የጅል ሥራ ከጀመሩ» አሉ ትናንት «ከመካና መዲና በስተቀር የምንተወዉ የሳዑዲ ግዛት አይኖርም።» አከሉ ሚንስትሩ። የሁለቱ ሹማምንት አዲስ ዛቻ እና አፀፋ ዛቻ፤ ከጦር መሳሪያ ሸመታዉ ጋር ተዳምሮ እስካሁን የሚደረገዉን ጦርነት ያብሰዋል ነዉ ሥጋቱ። የፖለቲካ ተንታኝ ዩሱፍ ያሲን ከሶሪያ እስከ የመን ያለዉ ጦርነት ከዛቻዉም በፊት ብሷል ባይ ናቸዉ። ኤርትራም ተሻግሯል።
                                  
ዩናይትድ ስቴትስ ኢራቅን ከወረረችበት ጊዜ ጀምሮ የሺዓ ሱኒዎች ግጭት፤ የኩርድ-አረቦች ሽኩቻ፤ የአል ቃኢዳ-አሜሪካኖች ጦርነት፤ የISIS ጦርነት እየተባለ የእስከያኔዋ ሐብታም፤ ትልቅ፤ ጥንታዊት ሐገር የዜጎችዋን ሕይወት፤  ሐብቷንም ትገብራለች። አስራ-አራት አመትዋ።አሜሪካ መራሹ የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃል ኪዳን ድርጅት (ኔቶ) ሊቢያን ከደበደበደ ወዲሕ ሰሜን አፍሪቃዊቱ ሐገር ጠፍታለች። አምስት-ዓመት ከመንፈቅዋ።ሶሪያ እየወደመች ነዉ። አምስት ዓመትዋ። የመን በእልቂት-ፍጅት፤ ስደት ረሐብ ቀዳሚዎችዋን መሽቀዳደም ከያዘች-ሰወስተኛ ዓመቷ ነዉ። የአፍቃኒስታንና የኢራቅ ወረራ አሜሪካኖችን ከከባድ ዕዳ እንደከተተ ሁሉ የየመኑ ጦርነት ለሪያድ ነገስታትን ዋኝተዉ የማይወጡት ባሕር ነዉ-የሆነባቸዉ። የሪያዱ ወኪላችን ስለሺ ሽብሩ እንደሚለዉ የተራዘመዉ ጦርነት ያሳሰባቸዉ የሳዑዲ ዜጎች ፈራ-ተባ እያሉም ቢሆንም ነገስታቶቻቸዉን ጎሸም-ጠቆም ማድረግ ጀምረዋል።
                                            
የሳዑዲ አረቢያ ነገስታት ተቃዋሚዎች ደግሞ የንጉስ ሰልማን አገዛዝ የመፈንቅለ-መንግሥት ሙከራ ተቃጥቶበት ነበርም ይላሉ። አቶ ዩሱፍ ያሲን። የሪያድ ገዢዎች የተገዢዎቻቸዉን አመፅና ጥያቄ ለማፈን ምጣኔ ሐብታዊ-ኪሳራዉን ማስተንፈስ እንደ ጥሩ ስልት ይዘዉታል። ስልቱን ገቢር ለማድረግ የዉጪ ዜጎችን መቅጣት።ቅጣቱ ገሚሱን ማባረር፤ በማይበረሩት ላይ አዳዲስ ግብር መጣል ነዉ። እንደገና ስለሺ። የጦር መሳሪያ ሸመታዉ ግን እንደቀጠለ ነዉ። የኢራኑ መከላከያ ሚንስትር «የሳዑዲ አረቢያ ገዢዎች አየር ኃይል ስላላቸዉ ሁሉንም ነገር ማድረግ የሚችሉ ይመስላቸዋል።» አሉ፤ የየመኑን ጦርነት መጥቀሳቸዉ ነበር።«ግን አልቻሉም» አከሉ።ብቻ ሳዑዲ አረቢያዎች ለሌላ ጦርነት ጦር መሳሪያ ይሸምታሉ።
ከነዳጅ ዘይት ሐብቷ በተጨማሪ ዘጠኝ ዓመት በዘለቀዉ የኢራን-ኢራቅ ጦርነት የተፈተነ ጠንካራ-ጦር፤ በቅጡ የተማረ ሰማንያ ሚሊዮን ሕዝብ ያላት ኢራን ሚሳዬሉን ራስዋ ታምርታለች። የጎደላትን ከሩሲያ ትገዛለችም። በዋሽግተኖች ግፊት የተባባሰዉ የሁለቱ ሐገራትተዘዋዋሪ ግጭት ጦርነት፤ ዛቻ እና ፉከራ ለፋርስ ባሕረ-ሠላጤ ትናንሽ ሐገራት ትላልቅ ሥጋት ነዉ-የሆነዉ።
                                      

Jemen Milizen entfernen Landminen platziert von Houthi-Rebellen
ምስል picture-alliance/dpa/STR
Raketenabschuss im Iran
ምስል picture alliance/AP/Isna
Iran Armee Streitkräfte Militär
ምስል Tasnim
Saudi-Arabien Marine-Übungen
ምስል Getty Images/AFP/F. Nureldine

ነጋሽ መሐመድ  

አዜብ ታደሰ