1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሩዋንዳና የቡሩንዲ ውዝግብ

ሰኞ፣ ነሐሴ 25 2007

ክስ ወቀሳ እስር ያስከተለው የብሩንዲ ቀውስ ፣ከጎረቤት ሩዋንዳ ጋር ወደ መጋጨትም እያመራ ነው። በርግጥ ሁለቱ ሃገራት ጦርነት አያሰጋቸውም ። ሆኖም ውዝግቡ በአካባቢው አደገኛ ቡድን የመፍጠር አዝማሚያ መኖሩን ይጠቁማል ።

https://p.dw.com/p/1GNds
Präsident von Ruanda Paul Kagame
ምስል Getty Images/AFP/Z. Abubeker

[No title]

የሩዋንዳው ፕሬዝዳንት ፖል ካጋሜ ስለ ብሩንዲው ፕሬዝዳንት ፕየር ንኩሩንዚዛ አወዛጋቢ ሶስተኛ የሥልጣን ዘመን ምን እንደሚያስቡ ምሥጢር አድርገውት አያውቁም። ባለፈው ግንቦት መጀመሪያ ላይ በትዊተር ባስተላለፉት መልዕክት «እንዴት አንድ ሰው ተስማማችሁም አልተስማማችሁም ባለሁበት እቆያለሁ ይላል« ይህ ትልቅ ችግር ነው» ብለው ነበር ። ካጋሜ ይህን ያሉት ንኩሩንዚዛ በይፋ ለሶስተኛ የሥልጣን ዘመን ራሳቸውን በዕጩነት ከማቅረባቸው በፊት ነበር። ንኩሩንዚዛ ሥልጣናቸውን ከተራዘመበት ካለፈው ሳምንት አንስቶ በሁለቱ ሃገራት መካከል ውጥረቱ ተብብሷል። ባለፉት ቀናት ውስጥ 30 የሚጠጉ ሩዋንዳውያን ብሩንዲ ውስጥ ታስረዋል። የታሰሩበት ምክንያት ደግሞ ግልፅ አልተደረገም። የዜጎቿን መታሰር የተቃወመችው ሩዋንዳ ምክንያቱ እንዲብራራላትና ዜጎቿም በአስቸኳይ እንዲለቀቁ ጠይቃለች። ከጥቂት ወራት አንስቶ በሁለቱ የምሥራቅ አፍሪቃ ጎረቤት ሃገሮች መካከል አለመተመመን ተፈጥሯል። ብሩንዲ ከከሸፈው የግንቦቱ መፈንቅለ መንግሥት ወዲህ ሩዋንዳ የንኩሩንዚዛን ተቀናቃኞች በመደገፍ ትወነጅላለች። የብሩንዲ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አልያን ንያሚትዌ ሐምሌ መጨረሻ ላይ ለኒው ዮርክ ታይምስ ጋዜጣ ከመፈንቅለ መንግሥቱ መሪዎች ቢያንስ ሦስቱ ሩዋንዳ ውስጥ ነው የሚኖሩት ብለዋል። ከዚህ ሌላ ቡሩንዲ ሐምሌ መጨረሻ ላይ በቡሩንዲ የስለላ መሥሪያ ቤት ሃላፊ በአዶልፊን ንሺሚሪማና ግድያ የምትጠረጥራቸውን ሰዎች ሩዋንዳ አሳልፋ እንድትሰጣትም ጠይቃለች። ሟቹ ንሺሚሪማና የንኩሩንዚዛ ቀኝ እጅ እና በንኩሩንዚዛ ተቃዋሚዎች ላይም ለተወሰዱ የኃይል እርምጃዎችም ተጠያቂም ነበሩ። ቡሩንዲ በሩዋንዳ ላይ ከምትሰነዝራቸው ክሶች ጥቂትም ቢሆን እውነት ይገኝበት ይሆን? በበርሊኑ የማዕከላዊ አፍሪቃ የአብያተ ክርስቲያናት ማስተባበሪያ ባልደረባ ጌዚነ አምስ ቡሩንዲ በሩዋንዳ ላይ ለምታቀርባቸው ክሶች ማስረጃ ማግኘቱ አስቸጋሪ ነው ይላሉ።
« ይህ በርግጥ ያልተጨበጠ ነው። እስካሁን ምንም ዓይነት ግልፅ መረጃ የለም። እውነታው በቡሩንዲ የፖለቲካ አለመረጋጋት ከተከሰተ ወዲህ ሩዋንዳ ውስጥ ከ270 ሺህ በላይ ስደተኞች ይገኛሉ። ከመካከላቸው የቡሩንዲ መንግሥት የሚያንገላታቸው ጋዜጠኞች መንግሥትን የሚተቹ እና የሚቃወሙ አሉበት። ሆኖም ከዚህ በመነሳት ሩዋንዳ የተቃዋሚዎችን እና መፈንቅለ መንግስት ያካሄዱት መቀመጫ እንዲሁም መፈንቅለ መንግሥት ያካሄደች አገር ናት ብሎ ለመደምደም የተጨበጠ ነገር አይደለም።»
በርግጥ ሩዋንዳ ቡሩንዲ የምትሰነዝረው ይህን መሰሉን ክስ አትቀበልም። ከዚያ ይልቅ ሩዋንዳ ቡሩንዲን «ለሩዋንዳ ነፃነት የዲሞክራሲ ኃይላት በምህፃሩ FDRL የተባሉትን» የሁቲ አማፅያን ሚሊሽያዎች ትደግፋለች ስትል ትወነጅላለች። ሩዋንዳ እነዚህ በምሥራቃዊ ኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ውስጥ ሚንቀሳቀሱት ሚሊሽያዎቹ ያሰጉኛል ትላለች። በቅርብ ሳምንታት ደግሞ አማፅያኑ ሩዋንዳና ቡሩንዲን በሚያዋስነው ድንበር ላይ ነበሩ የሚል ጭምጭምታም ተሰምቶ ነበር። ሆኖም ለዚህም ምንም ማረጋገጫ አልተገኘም። ይህን መሰሉ ውጥረት ሁለቱን ሃገራት ወደ ግልጽ ግጭት ይመራ ይሆን? ከቤልጂጉ የአንትቨርፕ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስና የሕግ ምሁር ፊሊፕ ራይንትየንስ ይህ የሚሆን አይመስላቸውም።
«እንደሚመስለኝ ካጋሜ ንኩሩንዚዛ ከሥልጣና እንዲወገዱ ይፈልጋሉ። ሆኖም ጥያቄው ይህን ለማሳካት ምን ያህል ይጓዛሉ ነው። አዎ እንደድሮው መቀጠል ይቻላል፤ ንኩሩንዚዛ ያሰቡት ተሳክቶላቸዋል እና አሁን ነገሮችን ይበልጥ አናባብስ ብለው ይወስኑ ይሆናል። ምክንያቱም ካጋሜ ለሚቀጥሉት 5 ዓመታት ከንኩሩንዚዛ ጋር ስለሚቆዩ የተበላሸውን አጥር ለመጠገን እየሞከሩ እንደ ቀድሞው እንዲቀጥል እንድድርግ ይሉም ይሆናል።»
በራይንትስ እምነት ከጥቂት ጊዜያት በኋላ የሁለቱ ሃገራት ግንኙነት ወደ ቀድሞው ደረጃ መመለሱ አይቀርም።
«አንድ ያልተጠበቀ ተለዋዋጭ ሁኔታ ካልተፈጠረ በስተቀር ማለትም በብሩንዲ መፈንቅለ መንግሥት ካልተካሄደ ወይንም ንኩሩንዚዛ ካልተገደሉ በሚቀጥሉት ጥቂት ሳምንታትና ወራት ሁኔታው ይረጋጋል ብዮ እገምታለሁ።»
ጌዚነ አምስ በበኩላቸው ለጋሽ ሃገሮች በተለይም የአውሮፓ ህብረት በአካባቢው ሊፈጠር የሚችል ተጨማሪ ግጭትን ለመከላከል የአካባቢው ሃገራት ይበልጥ እንዲተባበሩ እገዛ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል ።

Burundi Attentat Polizei
ምስል Getty Images/AFP/L. Nshimiye
Burundi Vereidigung Präsident Nkurunziza
ምስል Reuters/E. Ngendakumana

ኂሩት መለሰ

ሸዋዬ ለገሠ