ዉይይት፤ የኢትዮጵያ ለዉጥ በቀድሞ እስረኞች ዓይን
እሑድ፣ ሰኔ 10 2010ሕዳር 2008 ጊንጪ ኦሮሚያ መስተዳድር እንደዘበት የተጀመረዉ ሕዝባዊ አመፅ ተጠናክሮ፤ አድማሱን አስፍቶ ባለፉት 27 ዓመታት ኢትዮጵያ ዉስጥ ታይቶ የማይታወቅ ለዉጥ አምጥቷል። እስረኞች ተፈተዋል፤ የባለሥልጣናት ሹም ሽር ከሁሉም በላይ የጠቅላይ ሚንስትር ለዉጥ ተደርጓል። አዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር ሥልጣን ከያዙ ወዲሕ ደግሞ ተጨማሪ እስረኞች ተለቀዋል። የማይነኩ የሚመስሉት የጦር እና የስለላ ተቋማት አዛዦችን ጨምሮ የገዢዉ ፓርቲ ነባር ሹማምንት ከስልጣን ተወግደዋል።
ተሰደዉ የነበሩ ፖለቲከኞች ጥቂት ቢሆኑም ወደ ሐገር ገብተዋል። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተሰርዟል። የኢትዮ-ኤርትራን የድንበር ዉዝግብ ያስወግዳል የተባለዉን ሥምምነት ኢትዮጵያ ገቢር እንደምታደርግ ገዢዉ ፓርቲ ቃል ገብቷል። መንግሥት የሚቆጣጠራቸዉ የምጣኔ ሐብት ተቋማት በከፊል እንዲሸጡ ተወስኗል። ሌሎችም ፈጣን ለዉጦች እየተደረጉ ነዉ።
የዚያኑ ያክል በገዢዉ ፓርቲ ኢሕአዴግ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ ያሳርፋል የሚባለዉ ሕዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ (ሕወሓት) የኢሕዴግን ዉሳኔ በመቃወም ባለፈዉ ረቡዕ ማታ ያወጣዉ መግለጫ ለዉጡንና ተስፋዉን እንዳያጨናጉለዉ እንዳይደፋዉ አስግቷል።
የ«ውይይት» እንግዶቻችን ሕዝባዊዉ አመፅ ባሳደረዉ ጫና ከእስር የተለቀቁ የቀድሞ እስረኞች ናቸዉ። የእስር ቤት ቆይታቸዉ፤ የኢትዮጵያ ለዉጥ ትዝብታቸዉ እና የወደፊት ዕቅዳቸዉ የዛሬ ዝግጅታችን ትኩረት ነዉ። ሶስት ናቸዉ።ግን በእነደራሲ ደበበ ሰይፉ አገላለፅ ሶስትም አንድም ናቸዉ።
ነጋሽ መሐመድ