ከኒጀር የሚነሱት ስደተኞችና የአዉሮጳ የፍልሰት መርህ
ዓርብ፣ መጋቢት 15 2009
ይህ ገንዘብ ዓላማዉን አሳክቶ ይሆን? አፍጋግ ስደተኞችን ከኒጀር የአጋዴዝ ከተማ በሕገወጥ መንገድ ወደ ሊቢያ የሚያዘዋዉር የከተማይቱ ነዋሪ ነው። አፍጋግ ሥራ አጥ በሞላባት በአጋዴዝ በሰዎች አሸጋጋሪነት እጅግ ብዙ ገንዘብ አግኝቶአል። አሁን ግን የኒጀር መንግሥት የአዉሮጳ ኅብረት ጫና ካሳረፈበት በኋላ የስደተኞችን ሐገ ወጥ ዝዉዉር በይፋ አግዶአል። እንደ አፍጋግ ያሉ ሰዎችም እስር ይጠብቃቸዋል። እስካሁን በአጋዴዝ ከተማ በዚህ አይነት ተግባር ላይ የተሰማሩ ሰዎች ፍርድ ቤት ባይቀርቡም ከመቶ በላይ ሰዎች ታስረዋል። ግን አፍጋግ እንደሚለው፣ ክትትሉ ዋነኞቹን ሰው አሸጋጋሪዎች አልነካም። አፍጋግ በበኩሉ በዚህም አለ በዝያ ሰዎቹን ያጓጓዝኩት ስደተኞችን በሚያዘዋዉረዉ ተሽከርካሪ ነዉ ሲል ይገልጻል።
«የመታሰሩ እጣ የሚያጋጥመው ስደተኞቹን የሚያመጡትን፣ እስከ መጓጓዣዉ ድረስ የሚደብቋቸውን፣ ማለትም፣ ለሕገወጡ ዝውውር በዋነኝነት ተጠያቂ ያልሆኑትን ሾፌሮች ብቻ ነው። የሕገወጡ ዝውውር ኃላፊዎች ከመዲናዋ ኒያሜ ነው ትዕዛዛቸውን የሚያስተላልፉት። »
የኒጀር መንግሥት ያሳለፈዉ የእገዳ ዉሳኔ ከአጋዴዝን በረሃውን የሚቋርጠዉ የስደተኞች ቁጥር ለቀነሰበት ድርጊት ድርሻ ማበርከቱ በግልጽ አልታወቀም። የታወቀው ነገር፣ ሰው አዘዋዋሪዎች፣ ስደተኞች እና ፖለቲከኞች እንዳመለከቱት፣ ስደተኞችን በመኪና ለማዘዋወር የሚከፈለዉ ገንዘብ በእጥፍ መጨመሩ ነው። የአዉሮጳ ኅብረትና ዓለም አቀፉ የስደተኞች ጉዳይ ተመልካች ድርጅት፣ «አይ ኦ ኤም» ባወጡት ዘገባ እንደገለጹት፣ ሰዎች አሸጋጋሪዎች ስደተኞችን በበረሃማዉ መንገድ ለማዘዋወር ሌላ መንገድን ቀይሰዋል። ይኸው መንገድ ረጅምና ብዙ ፈተናዎች የተጋረጡበት መሆኑን የ «አይ ኦ ኤም» ባልደረባ ዡሱፔ ሎፕሬቴ ገልጸዋል።
« የኒጀር መንግስት ያሳረፈውን እገዳ ለማምለጥ ሲሉ በአንዳንድ መንገዶች አይሄዱም። በሌላ ረጅም መንገድ በኩል አድርገዉ ነዉ ቦታዉን የሚያልፉት። ይህ አንድ ወይም ሁለት ኪሎሜትር ሊያስጨምራቸው ይችላል፣ በረሃ በመሆኑም አንዳችም መንገድ የለውም።»
አካባቢዉ ላይ የሚገኙት ተቆጣጣሪ ፖሊስና ወታደሮችም ስደተኞችን ከሚያጓጉዙ ተሽከርካሪዎች ጉቦ እየተቀበሉ ስለሚያሳልፉዋቸው ሰዎች አሸጋጋሪዎች ስራቸዉን እንደቀጠሉ ነዉ። እርግጥ፣ የጀርመን ፊደራል መንግሥትና የአዉሮጳ ኅብረት በኒጀር ለፀጥታ ኃይላቱ ስልጠና እየሰጡ ቢሆንንም፣ ሙስና በስልጠናው ወቅት በይፋ የሚነሳ ርዕስ አልሆነም።
የአዉሮጳ ኅብረት በጎርጎረሳዊዉ 2016 ዓ,ም ወደ 750 ሚሊዮን ዩሮ የሚጠጋ ገንዘብ ለመስጠት ቃል ገብቶአል። ህብረቱ በዚህ ገንዘብ የተለያዩ ፕሮዤዎችን ለማቋቋም እቅድ ይዟል። ከፕሮጀክቶቹ መካከል አንደኛዉ ብዙ ገንዘብ እያስከፈሉ ስደተኞችን ለሚያዘዋውሩት ሰው አሸጋጋሪዎች አማራጭ የስራ ቦታ መክፈት የሚለዉ ነዉ።
በኒጀር የአዉሮጳ ኅብረት አምባሳደር ራዉል ማተስ ፓዉላ እንደሚሉት፣ በአጋዴዝ ግዛት ዉስጥ በፍጥነት ፍሬ ሊያስገኝ የሚችል አንድ የሥራ ንድፍ ተዘጋጅቷል። ሆኖም፣ የዚሁ እቅድ ውጤት እስካሁን በአጋዴዝ አልታየም። እርግጥ፣ ይላሉ የአዉሮጳ ኅብረት አምባሳደር ፓዉላ፣ ብዙዎቹ የአካባቢዊ ነዋሪዎች ፕሮዤው እንደሚጀምር ቢሰሙም፣ በተግባር ተተርጉሞ ያዩት ነገር የለም።
« ሰዎች ተነቃቃ የተባለውን ፕሮዤ አለማየታቸዉ ልክ ነዉ። ምክንያቱም ለአፍሪቃ ከተሰጠው ልዩ የገንዘብ ድጋፍ ተዋቅሮ የተነቃቃውን ፕሮዤ ተግባራዊ በማድረጉ የመጀመርያ ደረጃ ላይ ነዉ የምንገኘው።»
የጀርመን ፌዴራል ሬፓብሊክም ተመሳሳይ እቅድ ነው ያለዉ፣ ለኒጀር በሚቀጥሉት ሶስት ዓመታት 60 ሚልዮን ዩሮ ለመስጠት ቃል ገብቷል። በዚሁ ገንዘብ በአጋዴዝ ለበርካታ ነዋሪዎች የሥራ ቦታ ለመፍጠር ታስቧል። ጥያቄዉ ሰው አሸጋጋሪዎቹ በግብርና ወይም ቆሻሻን ዳግም ጥቅም ላይ በማዋሉ ስራ ላይ መሰማራትን ይቀበላሉ ወይ የሚለዉ ነዉ? እንደሚታወቀዉ እንደ አፍጋግ ያሉ ሰዎች ስደተኞችን በሕገወጥ እያዘዋወሩ እጅግ ብዙ ገንዘብ ስላገኙ፣ በአጋዴዝ የአካባቢ ፖለቲከኛ ባዉታሊ ችዌሪ፣ ሀሳቡን ተጠራጥረውታል።
«ሰዎችን በሕገወጥ መንገድ እያዛዋወረ በሳምንት ወደ 1500 ዩሮ ያገኝ ለነበረ ሰዉ ይህ የቀረበለት ሥራ ተቀባይነት አያገኝም። የፕላስቲክ ቆሻሻን በመሰብሰቡ ስራ አይሰማራም ወይም ለአዲሱ ሕግ የገለፃ ዘመቻ አያካሂድም። እውነታው ይህ ነዉ።»
አዜብ ታደሰ / የንስ ቦርቸር
አርያም ተክሌ