1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ከሁለት ወር ያነሰ ጊዜ የቀረዉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ

Merga Yonas Bula
ማክሰኞ፣ ሰኔ 6 2009

በኢትዮጵያ ለ10 ወራት የታወጀዉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ባለፈዉ ዓርብ ስምንተኛ ወሩን አጠናቅቋል። አዋጁ አላማዉ አድርጎ የተነሳዉ በአገሪቱ የተቀሰቀሰዉን ኃይል የቀላቀለ ተቃዉሞ ተከትሎ «ሰላም ለማስፈን» መሆኑን የመንግስት ባላስልጣናት ተናግረዋል።

https://p.dw.com/p/2edlD
Karte Äthiopien englisch

Less than two months left for SoE to expire - MP3-Stereo

ይህንንም ለማስፈፀምም የተቋቋመዉ ኮማንድ ፖስት በነዚህ ጊዜያቶች ዉስጥ በሽዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎችን እያሰረ እንደሚገኝና ስለ ሕገ-መንግስቱ ትምህርት ወሰዱ የተባሉት ደግሞ ሲለቀቁ ታይቶዋል።

የዶይቼ  ቬሌ ተከታታዮች «ሰላም ለማስፈን» ነዉ የተባለዉን ይህን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈፃፀም እንዴት እንደሚመለከቱት ጠይቀን ነበር።

ላለፉት ስምንት ወራት የሰብዓዊ መብት አያያዝ ሁኔታን በተመለከተ የአዳማ ነዋሪ የሆኑ አንድ ስማቸዉ እንዲጠቀስ ያልፈለጉ ግለሰብ  እየተባባሰ መቶዋል ይላሉ። በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ ቦታዎች ተዘዋዉረዉም የኮማንድ ፖስቱን ስራ መታዘባቸዉን እንዲህ ይናገራሉ።

የአዲስ አበባ ነዋር የሆኑና ስማቸዉ ግን እንዳይጠቀስ የፈለጉት ሌላዉ ግለሰብ በበኩላቸዉ  ለኮንስትራክሽን ሥራ ሲባል በተለያዩ በአገሪቱ ክፍሎች እንደሚዘዋዋሩ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል። አዋጁ «ሰላም የማስፈን» አላማዉ አድርጎ ቢነሳም እሱን ተገን አድርጎ «አንድ አንድ ሕገ ወጥ ነገሮች» ገሃድ ወቶ እንዲካሄድ አድርጎታል  ብለዋል።

ለሰባት ዓመት ፌዴራል ፖሊስ ሆኜ ሰርቻያለሁ ያሉንና አስተያየታቸዉን የሰጡን አንድ የደሴ ነዋሪ ናቸዉ።

እዛዉ በደሴ ነዋሪ የሆኑት ሌላዉ አስተያየት ስጭ በበኩላቸዉ አዋጁ በባህርዳርና በጎንደር መረጋጋትን  አምጥተዋል፣ ዉጤታማም ነዉ ብለዋል።

ይህንኑ ጉዳይ በተመለከተ በዶይቼ ቬሌ ፌስቡክ ላይ አስተያየት ከላኩልን ዉስጥ አዋጁ «ሰላም አስፍነዋል» የሚል አስተያየት የላኩልን አሉ። ሹሻይ በርሄ «አዋጁ አረጋግተዋል ሆኖም አሁንም መራዘም አለበት» ሲሉ አስተያየታቸዉን ሰንዝረዋል። አለሙ አብረሃ የሚል የፌስቡክ ስም የያዙት ደግሞ «ከአዋጁ በፊት ሕብረተሰቡ በሰላም ወጥቶ መግባት ይቅርና ቤቱ ዉስጥ ተቀምጦም ለሕይወቱና ለንብረቱ ምንም ዋስትና የለዉም ነበር አሁን እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን ሀገራችን ወደነበረችበት ሰላም ተመልሳ ማየታችን አስቸኳይ ግዜ አዋጁ ወሳኝና በትክክለኛ ወቅት የታወጀ ነዉ ባይ ነኝ» ስሉ አስተያየታቸዉን ጽፈዋል።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በተመለከተ በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ያለዉን አስተያየት ለመቀበል ያደረግነዉ ተደጋጋሚ ጥረት አልተሳካም። 

መርጋ ዮናስ 
አዜብ ታደሰ