1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያ፤ ግጭት ምክንያቱ እና መፍትሔዉ

እሑድ፣ መስከረም 14 2010

በየሥፍራዉ ደም ለሚያቃባዉ ግጭት ሐገሪቱ ከ1983 ጀምሮ የምትከተለዉ በብሔር፤ በጎሳ ወይም በቋንቋ ላይ የተመሠረተ ፌደራዊ ሥርዓትን ተጠያቂ የሚያደርጉ አሉ።ሌሎች ግን ይሕን አይቀበሉትም።በየስፍራዉ ለሚነሳዉ ግጭትም ገዢዉ ፓርቲ ኢሕአዴግ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት አልገዛም ማለቱን ዋና ምክንያት ያደርጉታል

https://p.dw.com/p/2kYLn
Karte von Äthiopien
ምስል DW/E.B. Tekle

ኢትዮጵያ፤ ግጭት ምክንያቱ እና መፍትሔዉ

ሰሞኑን በኢትዮጵያ ሶማሌ እና በኦሮሚያ መስተዳድሮች መካከል በተነሳዉ ግጭት እስካሁን ቁጥሩ በዉል ያልታወቀ ሰዉ ሕይወት ጠፍቷል።ሐብት-ንብረት ወድሟል።ከሐምሳ-አምስት ሺሕ በላይ ሕዝብ ተፈናቅሏል።ሰዎችን በተለይም ኦሮሞዎችን ከየነበሩበት ሥፍራ ማባረሩ እንደቀጠለ መሆኑ እየተዘገበ ነዉ።

ብዙ ጥፋት በማድረሱ የምሥራቅ ኢትዮጵያዉ ግጭት ጎላ እንጂ ባሌ እና ቦረና ዉስጥም በኦሮሞና በሶማሌ፤ በጉጂ ኦሮሞና በጉርጂ መካከል፤ አማራ እና ቅማንት፤ አማራና አፋር በገጠሟቸዉ ግጭቶች የሰዉ ሕይወት መጥፋቱ እየተነገረ ነዉ።ኢትዮጵያ፤ ከዚሕ ቀደም ያልነዉን ለመድገም የመጤ ወይም  የሠፋሪዎች እና የነባሮች ግጭት፤ የአማራና የኦሮሞ ግጭት፤ የወልቃይት ጠገዴ ወይም ፀገዴ ግጭት፤የኮንሶ ግጭት፤የወላይታና የሲዳማ ዉዝግብ፤ የአፋርና የኢሳ (ሶማሌ) ግጭት፤ የሱማሌና የኦሮሞ ግጭት፤ የኑዌርና የአኝዋክ ግጭት፤ ወዘተ እያለች፤ በግጭት ማግሥት ግጭቶን እያስተናገደች ሃያ ስድት ዓመት አስቆጥራለች።

በየአካባቢዉ የሚያነሱ የአስተዳደር እና የማንነት ጥያቄምዎችም እስከ ዛሬ ድረስ እንደቀጠሉ ነዉ።

በየሥፍራዉ ደም ለሚያቃባዉ ግጭት ሐገሪቱ ከ1983 ጀምሮ የምትከተለዉ በብሔር፤ በጎሳ ወይም በቋንቋ ላይ የተመሠረተ ፌደራዊ ሥርዓትን ተጠያቂ የሚያደርጉ አሉ።ሌሎች ግን ይሕን አይቀበሉትም።በየስፍራዉ ለሚነሳዉ ግጭትም ገዢዉ ፓርቲ ኢሕአዴግ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት አልገዛም ማለቱን ዋና ምክንያት ያደርጉታል።በድንበር ግዛት ይገባኛል፤በሐብት ባለቤትነት፤ በአስተዳደር እና በማንነት ጥያቄ ሰበብ የሚጫሩትንም ግጭቶች ገዢዉን ፓርቲ ወይም ለፓርቲዉ ያደሩ ወገኖችን የሚወቅሱ አሉ።

የኢትዮጵያ መንግስት ግን ለሁሉም ዓይነት ግችቶች ፀረ፤ ሠላም፤ ፀረ ልማትና የዉጪ የሚላቸዉን ኃይላት ይወነጅላል።

ግጭት፤ ዉዝግብ፤ አለመግባባቶቹን ለማስወገድ የተለያዩ ወገኖች የሚሰጡት የመፍትሔ ሐሳብ ለየቅል ነዉ።የዛሬ ዉይይታችንም የግጭቱን ዋና ዋና መክንያቶች እና መፍትሔ የሚባሉ እርምጃዎችን ባጫጭሩ ለመቃኘት ያለመ ነዉ።

ነጋሽ መሐመድ

ልደት አበበ