ኢትዮጵያ እና ኬንያ የግልገል ግቤ ግድብ ድርድር
ማክሰኞ፣ ግንቦት 23 2008የኢትዮጵያ መንግስት ግድቡ በቱርካና ወንዝ ላይም ሆነ አከባቢዉ በሚኖሩት ህብረተሰብ ጉዳት እንደማያደርስ፣ ግድቡ ከተጠናቀቀም በኋላ ኬንያ ከሃይሉ ምንጭ ተጠቃሚ ትሆናለች የሚል ጠንካራ አቋም ይዞዋል። የኬንያ ባለስልጣናት እና የተፈጥሮ ጥበቃ ተሟጋቾች ግን ግድቡ የቱርካናን ሃይቅ አድርቆ ለድርቅ፣ ረሃብ እና ግጭት ያስከትላል በሚል ነው የሚከራከሩት።
የሁለቱም ሃገራት መንግስታት ይህን ልዩነት በድርድር ለማስወገድ ቢሞክሩም ዉጤት ላይ መድረስ እንዳልቻሉ በመገናኛ ብዙኃን የወጡ ዘገባዎች ያሳያሉ። የኬንያ መንግስት ለችግር መፊቴ ለመፈለግ ድጋም ከኢትዮጲያ ጋር ድርድር እንደጀመረ የኬንያ የዉጭ ጉዳይ ሚንስትር አምና መሃመድ መናገራቸዉን ስታር የተሰኘዉ የኬንያ የዜና አዉታር ዘግቦታል።
የኢትዮጵያ መንግስት አቋም የሚተቹ ድርድሩ ተጀምሮ ሳይጠናቀቅ የግድብ ስራ መጀመር ማለት ለድርድሩ አቅሟን ለማጎለበት ነው በሚል ፕሮጄክቱ ከተጀመረ በኋላ የሚደረገዉ ድርድር ምን አይነት ድርድር ልሆን ይችላል ሲሉ ይተቻሉ። አቶ አበበ አይነቴ የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት እና ስልታዊ ጥናት ማዕከል የፖለቲካ ተንታኝ እንደ አካሄድ ድርድር መደረግ ያለበት ከጅምሩ መሆኑን ቢጠቅሱም፣ ትችቱ ትክክለኛ እንዳልሆነ ይናገራሉ። ስለዚህ የግድቡን ግንባታ ተከትሎ እየተፈጠረ ያለዉ «ግርታ እና ብዥታ» የተወሰኑ ፍላጎት ያላቸዉ የተሳሳተ መረጃ በማሰራጨታቸዉ ነዉ ይላሉ።
የቱርካና ሃይቅ በበራሃ የሚገኝ ስሆን በአከባቢዉ ለሚገኙ አርብቶ አደሮች እና በዚያ ለሚኖሩ ወደ ሶስት ሚልዮን የሚጠጉ ሰዎች ጥቅም እንደሚሰጥ ይነገራል። በሌላ በኩል ግን፣ የኬንያ መንግስትም ይህን ችግር ታሳቢ ቢያደርግም ፣ ከኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ሃይል ለመግዛት ዉል እንደተፈራረሙ እና ሁለቱንም አገር ኤሌክትሪክ ሃይል ለማገናኘት ፕሮጄክቱን በገንዘብ እየረዳ ያለዉ የአለም ባንክ መረጃ ያሳያል።
መርጋ ዮናስ
አርያም ተክሌ