ሰኞ፣ ኅዳር 12 2009
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈፃፀም አጣሪ ቦርድ በአዋሽ አርባ፣ በዝዋይ፣ በአላጌ፣ በዲላ፣ በጦላይ፣ በአዲስ አበባና በባህርዳር እስር ቤቶችና ወታደራዊ ካምፖች ዉስጥ የሚገኙትን እስረኞች የሰዉ መብት አያያዝ ሁኔታን በተመለከተ ከትላንት ጀምሮ የማጣራት ሂደቱ መጀመሩ ተጠቅሶአል።
የተዋቀሩት የቦርድ አባላት የገዢዉ መደብ አባላት መሆናቸዉ ቢገለጽም የሰዉ መበት ጥሰትና ተያያዥ ጉዳዮችን በማጣራቱ ሂደት ምንም ተፅኖ አያመጣም ማለታቸዉ ተሰምተዋል። አጣሪ ቦርዱም ቢሆን ወይም የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን «እዉነትን የሚደብቁ እንጂ እዉነትን አጣርቶ ለማኅበረሰቡ የሚያቀርቡ አይደለም» የያሉን መቀመጫዉን ብረስልስ ላይ ያደረገዉ ለሰብዓዊ መብቶች በኢትዮጵያ ማኅበር ዳይሬክተር አቶ ያሬድ ኃይለማርያም።
ዶይቼ ቬሌ ሲያነጋግራቸዉ ከነበረ የዓይን እማኞች ዉስጥ የሰዉ መብት ጥሰት መባባሱንና «እስር ቤትም ሞልቶ የቀቤሌ ሊቀመንበር ቤት ዉስጥም ሁሉ ሰዎች እየተሳሩ መሆናቸዉን» ከዛም አልፎ የደሕንነት አካልን በመፍራት ከቄያቸዉ ወደ ጫካ እየተሰደዱ መሆኑን በዘገባችን አሰምተን ነበር። አጣሪ ቦርዱ እንዲህ ያሉ ሁኔታዎችን እንዴት ሊያጣራ ይችላል ብለን የቦርዱን አባላቶች ለማገኘት ያደረግነዉ ሙከራ አልተሳካም።
የሰዉ መብት አያያዝን በተመለከተ የሚቀርበዉ ሪፖርት ምን ያህል ከአድሎ የፀዳ ይሆናል ብለንም የፌስቡክ ተከታታዮቻችንን አስተያየት ጠይቀን ነበር። «እራሳቸው የመረጡት አጣሪ ኮሚሸን እነሱ ጽፈው የሰጡትን ነው የሚያነበው እንጂ ለህሊናው ሲል አይሰራም፣ ምክንያቱም ህሊና ቢኖራቸው ኖሮ ይሄ ሁሉ ሰው ሲሞት ለምን ?ብለው በጠየቁ ነበር» ያሉን አሉ። በሌላ በኩል መንግስት ለታሳሪዎች ይቅርታ ማድረግ አለበት ሲሉ አስተያየታቸዉን የሰጡንም አሉ።
መርጋ ዮናስ
አዜብ ታደሰ