አደገኛው የአፍሪቃዉያን ስደት
ሐሙስ፣ መስከረም 12 2009«አጄንሲያ ሐበሺያ» የተባለው ስደተኞችን የሚረዳው ግብረ ሰናይ ድርጅት መሥራች እና ሃላፊ ኤርትራዊው አባ ሙሴ ዘርዓይ ለዶቼቬለ እንደተናገሩት፤ በግብፅም በርካታ ስደተኞች በእስር ቤቶች ይሰቃያሉ ። ባለፈዉ ሳምንት መጨረሻ «ፕሮ አዚል» የተባለው ለስደተኞች መብት የሚታገለው የጀርመን ድርጅት የ2016 ዓም የሰብዓዊ መብት ሽልማት» ያበረከተላቸው አባ ሙሴ ዘርዓይ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ በስደተኞች ጉዳይ ላይ የመከረው የተመድ ጉባኤ ለችግሩ አንድ መፍትሄ ያመጣል የሚል ተስፋ አላቸው።
አባ ሙሴ ዘርዓይ ባሕር አቋርጠው ወደ አውሮጳ ለመግባት የሚሞክሩ ስደተኞችን ሲታደጉ እና ለተገን ጠያቂዎች ድጋፍ ሲያደርጉ ከዐስር ዓመታት በላይ አስቆጥረዋል ። መቀመጫዉ ጀርመን ፍራንክፈርት የሚገኘዉ «ፕሮ አዚል» የተባለው ግብረ-ሰናይ ድርጅት ኤርትራዊው አባ ሙሴ ፣ላደረጉት አስተዋፅዖ ባለፈዉ ቅዳሜ እዉቅና በሰጠበት ሥነ-ስርዓት ላይ አባ ሙሴ«ለድምጽ አልባዎች ድምፄን ጎላ አድርጌ ማሰማት እሻለሁ» ሲሉ ተናግረው ነበር ። ስደተኞችን በተመለከተ አሁንም ቢሆን የተሻሻለ ነገር አይታይም ሲሉ ለዶቼቬለ በሰጡት ቃለ ምልልስ ተናግረዋል።
ትናንት ወደ አዉሮጳ አቅጣጫ ሜዲተራንያን ባህር ላይ ሲቀዝፍ የነበረ ጀልባ ተገልብጦ 42 ሰዎች መሞታቸዉን የግብፅ መንግስት አስታዉቋል። አባ ሙሴ ይህ ጉዳይ በመረጃ ደረጃ ደረሰን እንጂ እስካሁን ዝርዝሩን አልሰማንም እንዲያም ሆኖ በዚህ ዓመት ከ 1000 በላይ ሰዎች ሜዲተራንያን ባህር ላይ ሞተዋል ብለዋል።
በርካታ ኢትዮጵያዉያንና ኤርትራዉያን አሁንም ባህር አቋርጠዉ ወደ አውሮጳ እየተሰደዱ ነዉ ። ኬንያና ሱዳን ድንበራቸዉን አጥረዉ በተለይ ሱዳን በጃንጃዊድ ሚሊሽያ ስደተኞችን በማደንዋ ከጥቂት ወራት በፊት ጀምሮ ወደ አዉሮጳ የሚመጣዉ ኤርትራዊ ስደተኛ ቁጥር ቀንሷል ሲሉ አባ ሙሴ ዘርዓይ ተናግረዋል።
በሺዎች የሚቆጠሩ ስደተኞችን አጄንሲያ ሐበሺያ በተሰኘ የግብረ-ሰናይ ድርጅታቸው በኩል የሚረዱት ካቶሊካዊዉ ቄስ አባ ሙሴ ዘርዓይ ኒዮርክ ላይ ስደተኞች እና ፈላሲያን በተመለከተ ጉባዔ የተቀመጡት የዓለም መንግስታትና የመንግሥታት ተጠሪዎች አንድ መፍትሄ ላይ ይደርሳሉ የሚል እምነት እንዳላቸዉ ገልፀዋል።
አዜብ ታደሰ
ኂሩት መለሰ