1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የግብፅ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ

ማክሰኞ፣ ጥር 22 2010

መጭው የግብጽ ምርጫ ለተቃዋሚዎች አስቸጋሪ መሆኑ አየተገለጸ ነው፡፡የወቅቱ ፕሬዝዳንት አብዱል ፈታህ አልሲሲ በሚወዳደሩበት በዚህ ምርጫ ጠንካራ ተፎካካሪዎቻቸው ክውድድሩ ሜዳ አንድ በአንድ እየወጡ መምጣታቸው እያነጋገረ ነው፡፡

https://p.dw.com/p/2rlHY
Ägypten Präsident Abdel Fattah Al-Sisi
ምስል picture-alliance/dpa/K. Elfiqi

አነጋጋሪው የግብፅ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ

 በዚህ ወር ብቻ ዋነኛ ተፎካክሪ ይሆናሉ የተባሉት ጀነራል ሳሚ አናን በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡ሌሎች ሁለት ተፎካክሪዎች ደግሞ ራሳቸውን አግልለዋል፡
በመጭዉ  ሚያዚያ  አጋማሽ  በሚካሄደዉ  የግብፅ  ፕሬዝዳንታዊ  ምርጫ የቀድሞዉ ጀነራል  ሳሚ አናን አይወዳደሩም።ምክንያቱም ሰዉየዉ በቁጥጥር ስር ዉለዋልና። የአብዱል ፈታህ አልሲሲ ዋነኛ ተፎካካሪ ይሆናሉ ተብለዉ ይጠበቁ የነበሩት ጀነራል ሳሚ አናን ያለፈዉ ማክሰኞ በቁጥጥር ስር የዋሉት ያለ ፈቃድ በመወዳደር ወታደራዊ ደንብን  ጥሰዋል ፤በግብፅ ህዝብና በወታደራዊ ሀይሉ መካከል ግጭት ለመፍጠር ሞክረዋል በሚሉና  በሌሎች ተጨማሪ ክሶች ጥር 23 ቀን 2018 የምረጡኝ ዘመቻቸዉ ተቋርጦ በግብፅ ወታደራዊ ባለስልጣናት ወደ ወህኒ እንዲወርዱ ተደርጓል።

ይህንን ተከትሎም ሌላዉ ተወዳዳሪ የሰብዓዊ መብት ጠበቃዉ ካሊድ አሊ ከምርጫዉ ራሳቸዉን ማግለላቸዉን  ለደጋፊቻቸዉ ገልጸዋል።  በተመሳሳይ ሁኔታ የቀድሞዉ የአየር ሀይል ኮማንደር አህመድ ሻፊቅ በዚህ ወር መጀመሪያ ለዉድድር እንደማይቀርቡ አሳዉቀዋል። የወታደራዊ መኮንኑ ሻፊቅ ከምርጫ ራስን ማግለል ከጀርባዉ ጫና አለበት የሚሉም አሉ። ከበርሊን የፖለቲካና የሳይንስ ማዕከል የግብፅ ጉዳዮች ተመራማሪ ለሆኑት ስቴፋን ሮለ  ጉዳዩ ብዙ አላስደነቃቸዉም ። ለእርሳቸዉ ይህ የሚጠበቅ ነዉ።  
«ይህ ዕርምጃ የሚያሳየዉ ወታደራዊ ክፍሉ እንዴት ተቃዋሚወችን  ከነ ሙሉ ሀይላቸዉ ለማጥፋት እየሞከረ መሆኑን ነዉ።በተለይ ከራሱ ከወታደራዊ ክፍሉ የወጡትን።»

ከዚህ አኳያ ታዲያ የጄነራል ሳሚ አናን መታሰር ለሌሎቹ ወታደራዊ  አዛዦች ወደ ፖለቲካ እንቅስቃሴ እንዳይመጡ  መቀጣጫ  ነዉ ይላሉ ተመራማሪዉ ስቴፋን ሮለ። «ይህ ሌሎች ወታደራዊ አዛዦች በምንም መልኩ ቢሆን ደፍረዉ  ወደ ፖለቲካ እንቅስቃሴ መምጣት እንደሌለባቸዉ የሚያሳይ ምልክት ነዉ።»

Ägypten - Ex-Militärchef Sami Anan
ምስል picture alliance/AA/A. Ismail

ግብፅ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ እጩ ሆኖ ለመቅረብ ቢያንስ 25 ሺህ የደጋፊዎች ፊርማና  20 የፓርላማ ዓባላት ይሁንታ ማቅረብ የግድ ነዉ።መስፈርቱ  ከወዲሁ ከ3 ሚሊዮን በላይ ፊርማ ላሰባሰቡት ለወቅቱ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አልሲሲ ብዙ ከባድ ባይሆንም ፤የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ካሊድ አሊ ግን ቀላል አይደለም ይላሉ።በተለይ አልሲሲ በሚመሩት ፓርላማ የአባላቱን ይሁንታ ማግኜትም ይሁን« የጊዜ ገደቡ  ጫና ፈጥሮብናል» ሲሉ ተችተዋል።የተሰጠዉ የጊዜ ገደብም ቢሆን የሚያወላዳ አይደለም ሲሉ ይተቻሉ።በጎርጎሮሳዊዉ የዘመን ቀመር በ1981 የተገደሉት የቀድሞ የግብጽ ፕሬዝዳንት የአንዋር ሳዳት ልጅ መሀመድ አንዋርም  የፓርላማ አባላትን ይሁንታ በአጭር ጊዜ ማቅረብ «አስቸጋሪ ነዉ »ሲሉ ተመሳሳይ ቅሬታ ያነሳሉ።በዚህም ወታደራዊ ኃይሉ «መደበኛ መሰናክሎችን በማዘጋጀት  ዕጩወችን ለመቆጣጠርና እንቅፋት ለመፍጠር እየሞከረ መሆኑን የሚጠቁም ምልክት ነዉ» በሚል በአንዳንዶች ዘንድ እየተተቸ  ነዉ።«አልሞኒተር የተባለዉ» የበይነ መረብ ጋዜጣ  በቅርቡ ባወጣዉ ዘገባም ይህንኑ ተችቷል።

ጡረተኛዉ ጀነራል ሳሚ አናን በቁጥጥር ስር የዋሉት ግባፃዉያን  ተቃዉሞ የጀመሩበት 7ኛ ዓመት ላይ ነዉ።የቀድሞዉ ፀረ -ሙባረክ እንቅስቃሴ አቀንቃኝ ሙሀመድ አድል እንደሚሉት በነዚያ የተቃዉሞ ዓመታት የነበረዉ የተስፋ መንፈስ ብዙ አልቀጠለም።በተለይ በዴሞክራሲያዊ መንገድ ተመርጠዉ የነበሩት ሙሀመድ ሙርሲ ከታሰሩ ወዲህ የብዙ ግብፃዉያን  ተስፋወች ጠፍተዋል ሲሉ ለዶቼ ቬለ ገልጸዋል። 

የቀድሞዉ የሙባረክ ተቃዋሚና የአሁኑ የፖርላማ አባል ታሪክ አልኮሆሊ ግን የጣህሪር አደባባይ የተቃዉሞ ሰልፈኞች ከአብዮቱ ያተረፉት ነገር አለ ይላሉ።ቢያንስ «ማንም ሰዉ ፕሬዝዳንቱ ለዘልዓለም ይኖራል ብሎ አያስብም»፣ማንም አካልም ከ2011 በፊት ወደነበሩ  ሁኔታወች ይመለሳል ብሎ አያስብም ሲሉ ለዶቼ ቬለ ተናግረዋል። 

እሳቸዉ ይህን ይበሉ እንጅ ዓለም ዓቀፉ የሰብዓዊ ድርጅት ፤አምነስቲ ሀገሪቱ  በሰብዓዊ መብት አቀንቃኞችና በጋዜጠኞች ላይ ባነጣጠረ የጅምላ እስራትና ታሳሪወችን በማሰቃየት በከፋ የሰብዓዊ መብት ረገጣ ላይ መሆኗን በ2016/2017 ባወጣዉ ዓመታዊ ዘገባዉ አመልክቷል። 

Ägypten Parlamentswahlen
ምስል Reuters/M. Abd El Ghany

ተመራማሪዉ ስቴፋን ሮለም ሀገሪቱ ከሙባረክ አስተዳደር በከፋ ሁኔታ አፈና ለይ መሆኗን  ያስረዳሉ።  «በጣም አፋኝ ወደ ሆነ ዋታደራዊ አስተዳደር እያመራ ነዉ።በአፋኝ ርምጃወቹ ከጎርጎሮሳዊዉ 2011 በፊት ከታየዉ  የሙባረክ አስተዳደር በላይ ነዉ።

የፖሊስ አስተዳደሩም ቢሆን ከሁሉም በላይ አገልጋይነቱ ለፕሬዝዳንት አልሲሲና በዙሪያቸዉ ላሉ መሆኑን ያብራራሉ።

 የፖሊስ አስተዳደሩ ከሁሉም በላይ የሚያገለግለዉ ለፕሬዝዳንት አልሲሲ ለራሳቸዉና በዙሪያቸዉ ላሉ ጥብቅ ፖለቲካዊ ደህንነት ለማስጠበቅ ነዉ።ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ተቀባይነታቸዉ ቀንሷል።እንደማስበዉ ምናልባትም በመጀመሪያዉ ምርጫ ላይም በጣም ተወዳጅ አልነበሩም።ነገር ግን የተወሰነዉ የህብረተሰብ ክፍል ጠንካራ ሰዉ የሀገሪቱን ችግር ይፈታል ከሚል ተስፋ ጋር ተያይዞ ደስተኛ ነበር።በዚህ መሃል ብዙ ግብፃዉያን ማዘናቸዉ አልቀረም ምክንያቱም ኢኮኖሚያቸዉ በሚገርም ሁኔታ አሽቆልቁሏል።» 

ለዚህም ነዉ ።አብዛኛዉ የግብፅ ዜጋ ከተቃዉሞ ይልቅ  የዕለት ጉርሱን ለማግኘት ከዕለት ተዕለት ኑሮዉ ጋር  ትግል ላይ ነዉ የሚባለዉ። ይህ ምርጫ ዝምታዉን ለመስበር ጥሩ አጋጣሚ ነዉ የሚሉም አሉ። ነገር ግን የወታደራዊ ኃይሉ አፈና የዋዛ አይመስልም።

ክኒፕ ክሪስተን

ፀሀይ ጫኔ

ኂሩት መለሰ