ተጨማሪ ርዳታ ለኢትዮጵያ
ሐሙስ፣ ግንቦት 25 2008የአየር ንብረት ለዉጥን ተከትሎ በኢትዮጵያ በተለያዩ ክልሎች የተከሰተዉ እና 10,2 ሚልዮን ሰዎችን የአስቸኳይ የምግብ ርዳታ ጥገኛ ያደረጋቸውን ድርቅ እና መዘዙን ለመቋቋም ያስፈልጋል የተባለው የ1,4 ቢልዮን ዶላር ርዳታ እየተጠበቀ ባለበት ወቅት፣ ከአንድ ወር በፊት የታየው አስከፊ የጎርፍ አደጋ የብዙዎችን ህይወት በማጥፋት እና ሌሎችን እጅግ ብዙዎችን በማፈናቀል ችግሩን አባብሶዋል። በዚህም የተነሳ የኢትዮጵያ መንግሥት እና ግብረ ሠናይ ድርጅቶች የሚያስፈልገውን የርዳታ ገንዘብ ለማግኘት ጥረታቸውን አጠናክረው በመስራት ይገኛሉ።
በርዳታ እንዲቀርብ የተጠየቀውን የገንዘብ መጠን በተመለከተ የተመድ የአስቸኳይ ርዳታ አስተባባሪ መስሪያ ቤት፣ «ኦቻ»ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር በመሆን ባደረገው ክለሳ የገንዘቡ መጠን ከ1,4 ቢሊዮን ዶላር ወደ 1,52 ቢልዮን ዶላር ከፍ ማለቱን ትላንት ባወጣዉ ዘገባ አመልክተዋል። ከተጠየቀው ገንዘብ መካከል እስካሁን 831 ሚሊዮን ዶላር ብቻ ከኢትዮጵያ እና ለጋሽ አገሮች እንደተገኘ አክሎ አስታውቋል።
ለርዳታ የሚያስፈልገው ገንዘብ አሁን ወደ 1,5 ከፍ ያለበትን ምክንያት የኢትዮጵያ የብሔራዊ የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ኮምሽነር ምትኩ ካሳ ለአርሶአደር የሕህል ዘር አቅርቦት፣ ተጨማር የምግብ ርዳታ መግዛት እና የእንስሳት ጤና አጋልግሎት አስመልክቶ መጨመር መቻሉን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ትልቁን ድርሻ እየተወጣ እንዳለ ተደጋግሞ ቢነገርም የለጋሽ አገሮች ተሳትፎ ጥቂት እንደነበር ተዘግቦ ነበር። ኮሚሽነር ምትኩ ያ ተቀይረዋል ይላሉ።
«ኦቻ» በዘገባዉ እንዳመለከተዉ ድርቁ ላይ ተደርቦ የመጣዉ የጎርፍ አደጋ ያስከተለውን ችግር ለመቋቋም የኢትዮጵያ መንግስት ችግሩን ለመቋቋም ጠንክሮ እየሰራ መሆኑን በብሔራዊ የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ደበበ ዘዉዴ ተናግረዋል። እንደ «ኦቻ» ዘገባ 3,6 ሚሊዮን ሰዎች አስቸኳይ የጤና ርዳታ፣ እንዲሁም፣ የበልግ ወይም የክረምት ዝናብ በሚጀምርበት ጊዜ 5,6ሚሊዮን ገበሬዎች አስቸኳይ የእህል ዘር ያስፈልጋቸዋል።
መርጋ ዮናስ
አርያም ተክሌ