በጋምቤላ የደረሰዉ ጥቃት እና ትችቱ
ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 11 2008የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲ አንድነት መድረክ እና ሰማያዊ ፓርቲ በጋራ ባወጡት የጽሑፍ መግለጫ እና ለዶይቼ ቬለ በሰጡት ተጨማሪ ማብራሪያ መንግሥት ለዜጎቹ አስፈላጊዉን ጥበቃ ሳያደርግ ትጥቅ እንዲፈቱ በመደረጉ የተፈጠረ ችግር መሆኑን አመልክተዋል። የሀገሪቱ ምክር ቤት በበኩሉ ሁለት የሀዘን ቀናት እንዲታወጅ ወስኗል። ከደቡብ ሱዳን ጋር በሚጎራበተዉ የጋምቤላ ክልል 13 የተለያዩ ቀበሌዎች የሚኖሩ ከሁለት መቶ በላይ የኑየር ጎሳ አባላት ኢትዮጵያዉያን ሰሞኑን ከጎረቤት ደቡብ ሱዳን በመጡ ታጣቂዎች መገደል መንስኤዉ አካባቢዉን የሚከላከል ኃይል ባለመኖሩን መሆኑን የክልሉ ተወላጆችም ይገልጻሉ። የግድያዉ ሰለባዎች በአብዛኛዉ ሴቶች፣ አረጋዉያን እና ሕፃናት መሆናቸዉን ከአካባቢዉ የሚወጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ። ከሟቾቹ በተጨማሪም ከአንድ መቶ የሚበልጡ ሕፃናትም በታጣቂዎቹ ታፍነዉ መወሰዳቸዉ፤ ከ 2000 በላይ ከብቶችም መዘረፋቸዉ ተገልጿል። ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት ጥቃት አድራሾቹ በደቡብ ሱዳን ጆንግሌ እና አፐር ናይል ግዛቶች የሚገኙት የሙርሌ ጎሳ አባላት ናቸዉ። የሚኖሩበት አካባቢ በጦር መሣሪያ መጠቅለቅለቁም ተጠቅሷል። የጋምቤላ ክልል በሺህዎች የሚቆጠሩ ደቡብ ሱዳናዉያን ከሀገራቸዉ ጦርነት ሸሽተዉ የጠጉበት ስፍራ ነዉ።
ዮሐንስ ገብረ እግዚአብሔር/ናትናኤል ወልዴ
ሸዋዬ ለገሠ
ነጋሽ መሐመድ