1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በጀርመን የሽብር ተጠርጣሪዉ ራሱን ማጥፋቱና የቀሰቀሰዉ ቁጣ

ሐሙስ፣ ጥቅምት 3 2009

ባለፈዉ ሳምንት መጨረሻ በጀርመን ኬምኔትዝ ከተማ በጥገኝነት ይኖር የነበረ ሶርያዊ ከፍተኛ ጥቃት ሊያደርስ ነዉ በሚል የሽብር ጥርጣሪ ቤቱ ተፈትሾ ተቀጣጣይ ፈንጂ መስርያ ቁስ ከተገኘበትና ከተሰወረበት በሃገሩ ልጆች ተይዞ በፖሊስ ቁጥጥር ከዋለ ከቀናት በኋላ በታሰረበት ክፍል ዉስጥ ራሱን መግደሉ ተገለፀ።

https://p.dw.com/p/2RBoX
Deutschland Terrorverdächtiger Al-Bakr erhängt in Zelle aufgefunden
ምስል picture-alliance/dpa/S. Willnow

Sachsen - Al-Bakr - MP3-Stereo

የ 22 ዓመቱ ሶርያዊ ጃባር ኧል-ባክር ምንም ዓይነት ጉዳት ሳያደርስ መያዙ የጀርመንን ነዋሪ ያስደሰተ ቢሆንም ከሁለት ቀናት በኋላ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ሳለ ራሱን ገደለ መባሉ ግን  ቁጣን ቀስቅሶአል፤ ከፍተኛ የመነጋገርያ ርዕስም ሆኖ ነዉ የዋለዉ።

Deutschland Syrer nach Sprengstoffund in Chemnitz gesucht
ራሱን ያጠፋዉ ሶርያዊ ጃባር ኧል-ባክርምስል picture-alliance/dpa/Polizei Sachsen

 

በጀርመንዋ ላይፕዚግ ከተማ  እስር ቤት ዉስጥ የነበረዉ የ 22 ዓመቱ ሶርያዊ ተጠርጣሪ ጃባር ኧል-ባክር  በፖሊስ እጅ ዉስጥ ሳለ ራሱን የማጥፋቱ ዜና የጀርመንን ነዋሪ በጥዋት የቀሰቀሰ፤ ያስደነገጠም ዜና ነበር። በምርመራ እስር ላይ የነበረዉ ተጠርጣሪ ሶርያዊ በአስተርጓሚ ምርመራ ይካሄድበት እንደነበር፤ የእምሮ ድጋፍ የሚያደርግለት ባለሞያም በየጊዜዉ ይከታተለዉ እንደነበር፤ በየ 30 ደቂቃዉ በነበረበት ክፍል ዉስጥ ቁጥጥር ይደረገበት እንደነበርና ግለሰቡ በጣም ፀጥተኛ ይመስል እንደነበር፤ ግን ምግብም ሆነ የሚጠጣ ፈሳሽ ነገር አልወስድም ብሎ ረሃብ አድማ ላይ እንደነበር የእስር ቤቱ ባለስልጣናትና የላይፕዚግ ከተማ አቃቤ ሕግ በሰጡት ጋዜጣዉ መግለጫ ገልፀዋል። በሽብር የተጠረጠረዉ ሶርያዊ ራሱን ይገላል የሚል ጥርጣሪም ፍጹም እንዳልነበር ነዉ የተነገረዉ።  የላይፕዚግ  ከተማ እስር ቤት ባለስልጣናት እና የከተማዋ አቃቤ ሕግ በሰጡት ጋዜጣዉዊ መግለጫ ለምርመራ እስር ላይ የነበረዉ ሶርያዊ ተጠርጣሪ ኧል-ባክር የለበሰዉን ቲሸርት ተልትሎ ራሱን መስቀሉንና ፤ ፖሊስ ነፍሱ ሳትወጣ ደርሶበት ሕይወቱን ለማትረፍ ለ30 ደቂቃ ሙከራ መደረጉን ቢሆንም ዉጤት አለመገኘቱን ተናግረዋል።  

« በሽብር ተግባር የተጠረጠረዉ ጃባር ኧል-ባክር  ላይብሲግ የሕግ ክትትል በሚደረግበት እስር ቤት ራሱን አጥፍቶአል።  ይህ ሊከሰት የማይገባዉ ጉዳይ ነበር፤ እንዳለመታደል ሆኖ ግን ይህ ሁኔታ ተከሰተ። ምንም እንኳ ተጠርጣሪዉ ራሱን እንዳይገል ብሎም ሕይወቱን ለማትረፍ የቻልነዉን ሁሉ ብናደርግም ጥረታችን ግን አልተሳካም። »

ለ 22 ዓመቱ ሶርያዊ ተጠርጣሪ ጃባር ኧል-ባክር  ተመድበዉ የነበሩት ጠበቃ አሌክሳንደር  ሁብነር  በበኩላቸዉ ጉዳዩ እጅግ እንዳስደነገዘቸዉና ተጠርጣሪዉ ታሳሪ ጃባር ኧል-ባክር ራሱን ይገላል የሚል ጥርጣሪ እንደነበራቸዉ ነዉ የገለፁት።     

« በርግጥ ብዙ ጊዜ እንደሚታየዉ እስረኞች እራሳቸዉን ለማጥፋት ሙከራ እንደሚያደርጉ ይታወቃል። ነገር ግን ይህ የተከሰተዉ ጉዳይ እጅግ አስደንጋጭ ነዉ። ተጠርጣሪዉ ሊሰራ ባቀደዉ ተግባርና በቀረበበት ክስ መሰረት ራሱን ይገላል የሚል ጥርጣሪም ነበረኝ ። ለምሳሌ በእስር ላይ ሳለ የምግብ ያለመብላት አድማና አድርጎም ነበር። »

የጀርመን ሃገር አስተዳደር ሚኒስትር ቶማስ ዴሚዜር ከጋዜጣዊ መግለጫዉ በፊት « ZDF» ለተባለዉ የሃገሪቱ ሌቭዥን ቀርበዉ በሰጡት ቃለ ምልልስ ነገሩ በአስቸኳይና በግልፅ ተጣርቶ ይቅረም ሲሉ ትዕዛዝ አስተላልፈዋል።      

Deutschland PK zum Tod des Terrorverdächtigen Al-Bakr
ጋዜጣዊ መግለጫ ምስል picture-alliance/dpa/A. Burgi

«ትናንት ስለደረሰዉ ነገር የፍርድ ቤት ባለሥልጣን ግልፅና ፈጣን የሆነ መልስ እንዲሰጥ እንጠይቃለን። እርግጠኛ ሆኜ መናገር የምችለዉ አስገራሚና አሳሳቢ የነበረዉን ጉዳይ የተከሰተዉ ሁኔታ እጅግ ከባድ ያደርገዋል። ከዝያም በመለጠቅ በታቀደዉ ጥቃት ላይ የነበረዉን ምርመራና ከታቀደዉ ጥቃት በስተጀርባ ማን እንደነበር ለማወቅ ነገሩን ከባድ ያደርገዋል። ያም ሆነ ይህ አሁን የተከሰተዉን ጉዳይ ፈጣን መልስ እጠብቃለን። »     

በአስቸኳይ ነገሩ እንዲጣራ የጠየቁት የሃገር አስተዳደር ሚኒስትሩ ብቻ ሳይሆኑ የሃገሪቱ የፖሊስ መምርያ፤ ባለስጣናትን እንዲሁም ታዋቂ ፖለቲከኞች በተለያዩ የማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ቁጣቸዉን በመግለፅ እስር ቤቱ ላሳየዉ ጥንቃቄ ጉድለት ማስረጃዉን በአፋጣኝ ይዞ እንዲቀርብ ጠይቀዋል።

አዜብ ታደሰ

ነጋሽ መሐመድ