በአማራ ክልል ግጭት መባባሱ
ረቡዕ፣ ነሐሴ 25 2008
በዚህ በያዝነዉ ሳምንትም ባህር ዳር፣ በዳንግላ፣ በጋይንት፣ በደብረታቦርና ሌሎች አከባቢዎች ተቃዉሞዉና ከፀጥታ ኃይላት ጋር ግጭቱ እንደቀጠለ ከዚሁ አካባቢዎች ያገኘናቸዉ ምንጮች ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል።
የባህር ዳር ነዋሪ መሆናቸዉን የተናገሩትና ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የፈለጉት ግለሰብ በከተማዋ «መዉጫና መግብያ የለም» ሲሉ የባህር ዳርን ወቅታዊ ሁኔታ እንድህ አብራርተዋል።
የአገሪቱ ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ትላንት በሰጡት መግለጫ እነዚህ ወጣቶች «ፀረ ሰላም» ናቸዉ፤ ስለዚህም «የማያደግም ርምጃ» መወሰድ አለበት ካሉ በኋላ ወደ ከተማዋ ትላንት ወታዳር መለካቸዉን እኝሁ ነዋሪ ተናግረዋል። ሌላ የከተማዋ ነዋሪ በበኩላቸዉ ማኅበረሰቡ የሥራ ማቆም አድማ እንደመታና ዛሬ አብዛኛዉ ሰዉ ቤቱ እንደዋለ ተናግረዋል።
የዳንግላ ነዋሪ መሆናቸዉን የተናገሩትና ስማቸዉም እንዳይጠቀስ የፈለጉት ግለሰብ ደግሞ በከተማዋ ያሉት የፀጥታ ኃይላት መፈናፈኛ አሳጥተዉናል ይላሉ።
ሌላኛዉ የጋይንት ተወላጅ እሁድ እለት ሰላማዊ ሰልፍ እንደነበረ ተናግረዉ ከፀጥታ ኃይሉ ጋር በተፈጠረ ግጭት የሰዉ ህይወት ጠፍተዋል ብለዋል። እኝ የጋይንት ነዋሪ እንደሚሉት መንግሥት ከማኅበረሰቡ ጋር በችግሩ ዙርያ መወያየት ቢፈለግም ማኅበረሰቡ የታጠቀ የአጋዚና የፌደራል ኃይል እንዲወጣ ቢያዝም ሊስማሙ አልቻሉም ብለዋል።
ባህር ዳርን ጨምሮ ሌሎች ወረዳዎች ላይ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት አገልግሎት እንዳይሰጡ ተገደዉ እንደነበርና ሌሎች ቦታ ሰለማዊ ሰልፍ ቢካሄድም አንዳንዶች የሰላማዊ ዜጎች ንብረት ላይ ጥቃት እንዳደረሱ የክልሉ መንግሥት ቃል-አቀባይ አቶ ንጉሱ ጥላሁን ለዶይቼ ቬሌ ተናግራዋል።
ከዶቼ ቬሌ ድረ ገፅ ተከታታዮች መካከል አንዳንዶች መከላከያ ሠራዊት ቦታዉ ላይ ማሰማራት «ለሀገራዊ ደኅንንነት ሲባል መታወጁ አስደስቶኛል» ሲሉ፣ ሌሎች ደግሞ «ሰው መግደል፣ማሰርና ማሳደድ ዘላቂ መፍትሄ አይሆንም። መከላከያ ወታደርም ቢሆን የራሱን ዜጎች መግደሉ ተገቢ አይደለም» ሲሉ አስተያየታቸዉን አጋርተዉናል።
መርጋ ዮናስ
አዜብ ታደሰ