ስለሥጋ ደዌ ግንዛቤና ህክምና
ማክሰኞ፣ መስከረም 10 2009በቀድሞ ስያሜዉ የልዕት ዘነበወርቅ ሃኪም ቤት ወይም የዛሬዉ አለርት ትኩረቱን ሥጋ ደዌ ላይ አድርጎ የሚሠራ ሆስፒታል ነዉ። አለርት በየጊዜዉ አዳዲስ የበሽታዉ ተጠቂዎችን አሁንም እየተቀበለ እንደሚያክም የሀኪም ቤቱ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዓለም ሰገድ ጫኔ ያስረዳሉ። ዋና ትኩረቱ የሥጋ ደዌ ላይ ቢሆንም ሌሎች ህክምናዎችንም እንደሚሰጥም ይናገራሉ። የሆስፒታሉ ሜዲካል ዳይሬክተር ዶክተር ሰሎሞን ቡሳ ሃኪም ቤቱ በአሁኑ ጊዜ በሚሰጠዉ ዘርፈ ብዙ የሕክምና አገልግሎት ምክንያት በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ሕዝብን እንደሚያስተናግድ አረጋግጠዋል።
በመላዉ ዓለም የሥጋ ደዌ ዘመናትን ያስቆጠረ በሽታ መሆኑን መረጃዎች ይጠቁማሉ። ስለህክምናዉ አጀማመር ፍንጭ የሚያሳዩ ማስረጃዎች ባይገኙም አንዳንድ ሳይቲስቶች ግን ቅድመ ልደተ ክርስቶስ 1550 ላይ ጥንታዊ የግብጽ ጽሆፎች ይህን እንደሚጠቁሙ ይጠቅሳሉ። በኢትዮጵያ ያለዉን ታሪክ ዶክተር ሰሎሞን ጠቅሰዋል።
አቶ አብይ አባተ በኢትዮጵያ የሥጋ ደዌ ተጠቂዎች ማኅበር የፋይናስና አስተዳደር ኃላፊ ናቸዉ። በማኅበራት የተደራጁት የሥጋ ደዌ ተጠቂዎች ስለሚያገኙት ሕክምና አብራርተዋል። አክለዉም በሰባት ማኅበራት የተሰባሰቡት የበሽታዉ ተጠቂዎች በአሁኑ ጊዜ ሕክምናዉን በየአካባቢያቸዉ ማግኘት መቻላቸዉን ይገልጻሉ።
የሥጋ ደዌ በዘር አይተላለፍ እንጂ ከሰዉ ወደ ሰዉ ሊጋባ የሚችል በሽታ መሆኑን ያብራሩት ዶክተር ሰሎሞን እንዴትነቱንም አስረድተዋል። የዓይን ስፔሻሊስት የሆኑት ዶክተር ሰሎሞን ከ30 ዓመታት በላይ በአለርት ሆስፒታል በሥጋ ደዌ የተጠቁ ወገኖችን እያከሙ መቆየታቸዉን ይናገራሉ። በንክኪ በሽታዉ የሚጋባ ቢሆን ኖሮ አሉኝ፤
ለረዥም ዓመታት በአለርት ሆስፒታል ያገለገሉት ዶክተር ሰሎሞን ቡሳ፤ ለሥጋ ደዌ ተጠቂዎች የሚቀርብ የመድኃኒት እጥረት እንደሌለ ነዉ የሚያስረዱት። ግን በዚህ ቆይታቸዉ የታዘቡት አልጠፋም። የሥጋ ደዌ ተጠቂ ወገኖች በማኅበራት መሰባሰባቸዉ አንድ ነገር ቢሆንም በኅብረተሰቡ ዉስጥ ሳይገለሉ ለመኖር የስነልቡና ድጋፍ ያገኙ ይሆን? አቶ አብይ ጥረታቸዉን ገልጸዉልናል። ሙሉ ዝግጅቱን ከድምጽ ዘገባዉ ያድምጡ!
ሸዋዬ ለገሠ
ኂሩት መለሰ