ማዳበሪያና የህዝብ አስተያየት
ማክሰኞ፣ ጥር 17 2008የአፈርን ለምንነት ለማሻሻል ማዳበሪያ መጠቀም ለገበሬዉ አዲስ አይደለም። ስለማዳበሪያዉ ዓይነት እና አጠቃቀም ግን የተለያዩ አስተያየቶች ይሰነዘራሉ። ወትሮ ገበሬዉ ተፈጥሯዊ መንገድን ተከትሎ የሚያርሰዉን መሬት ለምነት ለማሻሻል የተለያየ ስልት ሲጠቀም ኖሯል። በአሁኑ ጊዜ ደግሞ በሰዉ ሰራሽ ስልት የተዘጋጀ ማዳበሪያ በስፋት ሥራ ላይ ዉሏል። ያነጋገርናቸዉ ወገኖች ዘመናዊዉን ማዳበሪያ በሚመለከት ያላቸዉ አስተያየት አሉታዊም አዎንታዊም ነዉ።
ተሞክሮም ሆነ አስተያየታቸዉን እንዲያካፍሉን ከጠየቅናቸዉ አብዛኞቹ ገበሬዉ ማሳዉን እያስተዋለ በተፈጥሯዊ ዘዴ የመሬቱን ለምነት አሻሽሎ ምርቱን ያሳድግበት የነበረዉ ስልት በሰዉ ሠራሽ ማዳበሪያ መተካቱን ይተቻሉ። በነገራችን ላይ ሰዉ ሰራሹን ማዳበሪያ የሚነግደዉ ዓለም በየቤቱ የማዳበሪያ አጠቃቀም መጠን እና አኳኋኑን ጨምሮ ከፍተኛ ጥንቃቄ ያደርጋል። ለሽያጭ የሚገርቡ ምርቶችም በተፈጥሯዊ መንገድ የበቀሉ እና ያደጉ ከሆኑ ዋጋቸዉ ዉድ ነዉ። ያንን የሚመገቡ ደግሞ ጤነኛ የአመጋገብ ስልት የሚከተሉ አዋቂዎች ተብለዉ በአርአያነት ይታያሉ። ይደነቃሉ። አፈሩ የተዘራበትን እንዲያበቅል ብቻ ሳይሆን ለፍሬ እንዲያበቃ ባለሙያዎች እንደሚሉት በቂ ክብካቤ እንደሚያስፈልገዉ አይካድም፤ ማዳበሪያ አጠቃቀሙ ላይ ግን ጥንቃቄ ማድረጉ ተፈጥሮዉን መጠበቅ ነዉ። ሰብል ማፈራረቁ፤ አንዱን ዓመት ጦም አሳድሮ እያሰለሱ ማምረቱ፤ ከጓዳም ሆነ ከበረት የሚወጣዉን ዉዳቂ እየቀበሩ አብላልቶ አፈሩ ላይ ማፍሰሱን ኑሮዉ ለሆነዉ ብልህ ገበሬ መንገር ደግሞ ለቀባሪዉ ማርዳት ነዉ።
ሸዋዬ ለገሠ
አርያም ተክሌ