1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሶሻል ዲሞክራቶች ለጥምር መንግሥት ድርድር ተስማሙ

እሑድ፣ ጥር 13 2010

በቦን ከተማ ውስጥ የተሰበሰበው በጀርመን ምክር ቤት 2ኛ አብላጫ ድምጽ ያለው የሶሻል ዲሞክራቲክ ፓርቲ (SPD) ለግዙፉ ጥምር መንግሥት ድርድር ፍቃደኝነቱን ዛሬ ገለጠ። ወደ 600 የሚጠጉ የፓርቲው ተወካዮች በጉዳዩ ላይ ድምጽ ሰጥተዋል። 362ቱ የድጋፍ 279ኙ ደግሞ የተቃውሞ ድምጻቸውን ሰጥተዋል።

https://p.dw.com/p/2rG6l
Außerordentlicher SPD-Parteitag
a Abstimmung
ምስል Reuters/W. Rattay

በቦን ከተማ ውስጥ የተሰበሰበው በጀርመን ምክር ቤት 2ኛ አብላጫ ድምጽ ያለው የሶሻል ዲሞክራቲክ ፓርቲ (SPD) ለግዙፉ ጥምር መንግሥት ድርድር በጠባብ ልዩነት ፍቃደኝነቱን ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት ገለጠ። ወደ 600 የሚጠጉ የፓርቲው ተወካዮች በጉዳዩ ላይ ድምጽ ሰጥተዋል። የጥምር መንግሥት ድርድሩ እንዲጀመር በተደረገው የድምጽ አሰጣጥ ሥነ-ሥርዓት ከ600 ተወካዮች መካከል 362ቱ ድጋፋቸውን ሲሰጡ 279ኙ ደግሞ ተቃውመዋል። 

ሶሻል ዲሞክራቶቹ ባለፈው መስከረም ወር በተደረገው የጀርመን ምክር ቤት ምርጫ ሁለተኛ አብላጫ ድምጽ አግኝተዋል። ሆኖም ያገኙት ድምጽ ከጎርጎሮሳዊው 1949 ወዲህ ዝቅተኛ ነው ተብሏል፡፡ ይህ ውጤት ከዚህ ቀደም ከክርስቲያን ዲሞክራቲክ ኅብረት (CDU) እና የባዪርን ግዛቱ የክርስቲያን ሶሻል ኅብረት እህት ፓርቲው ጋር ያደርጉት የነበረውን የጥምር መንግስት ምስረታ ድርድር መለስ ብለው እንዲመለከቱ አስገድዷቸዋል፡፡ በመራኂተ-መንግሥት አንጌላ ሜርክል የሚመራው የክርስቲያን ዲሞክራቶቹ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ያደረገው የመንግስት ምስረታ ድርድር መክሸፉ ግን ሶሻል ዲሞክራቶቹ በዋና ተቃዋሚ ፓርቲነት ለመቆየት የደረሱበትን ውሳኔ እንዲያጥፉ አድርጓቸዋል፡፡ ሹልዝ ለፓርቲው ተወካዮች ዛሬ ሲናገሩ ያለው ምርጫ “ወይ ጥምር መንግስት ለመመስረት መደራደር ነው አሊያም አዲስ ምርጫ መካሄድ ነው” ብለው ነበር፡፡ “አዲስ ምርጫ ትክክለኛው መንገድ አይደለም” ሲሉም አክለዋል፡፡ ከሜርክል ፓርቲ ጋር የሚደረገው የጥምር መንግስት ምስረታ ድርድር ቀደም ብሎ ስምምነት ላይ በተደረሰባቸው የአሠሪና ሠራተኛ ሕግ፣ የጤና ስርዓት እና የስደተኛ ቤተሰቦችን ማገኛነት ጉዳዮች ላይ መሻሻሎች ለማምጣት ያስችላል ብለዋል፡፡ ሹልዝ ወደ ጀርመን የሚገቡ ስደተኞች ላይ የቁጥር ገደብ እንደማያስቀምጡ ሲናገሩ ከፓርቲው ተወካዮች ጭብጨባ ተለግሷቸዋል፡፡

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ተስፋለም ወልደየስ