24 ኛው የአፍሪቃ ሕብረት የመሪዎች ጉባዔ
ዓርብ፣ ጥር 22 2007ማስታወቂያ
24 ተኛው የአፍሪቃ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ለክፍለ ዓለሙ የሰላምና ፀጥታ ጉዳዮች ቅድሚያ ትኩረት በመስጠት ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ ተጀመረ ።በጉባኤው ላይ በናይጀሪያ እየተጠናከረ የሄደውን የቦኮሃራም ጥቃት መመከት የሚያስችል የጋራ ኃይል እንዲቋቋም ጥሪ ቀረቧል ። ለዚሁ ዓላማ ከ5 የአካባቢው ሃገራት የሚውጣጣ 7500 ወታደር እንዲሰማራ የአፍሪቃ ህብረት የሰላምና የጸጥታ ምክር ቤት ጠይቋል። የህብረቱ ኮሚሽን ሊቀመንበር ንኮሳዛና ድላማኒ ዙማ ባሰሙት ንግግር ከናይጀሪያ አልፎ ወደ አካባቢው አገራትም እየተስፋፋ በመጣው በቦኮሃራም ላይ የጋራ ውጤታማና ወሳኝ እርምጃ መውሰድ እንደሚገባ አሳስበዋል ። ነገ ያበቃል ተብሎ የሚጠበቀው የመሪዎቹ ጉባኤ በደቡብ ሱዳንና በማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ በሚካሄደው ጦርነት እንዲሁም በድርቅና ምዕራብ አፍሪቃን ባጠቃው ኤቦላ ላይም ይነጋገራል ። በዚሁ ጉባኤ ላይ የዚምባብዌው ፕሬዝዳንት ሮበርት ሙጋቤ በዙር የሚደርሰውን የአፍሪቃ ህብረት ሊቀመንበርነት ከሞሪቴንያው አቻቸው ሞሀመድ ኡልድ አብደል አዚዝ ተረክበዋል ። የጉባኤውን ሂደት የተከታተለው የአዲስ አበባው ዘጋቢያችን ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ ዝርዝሩን ልኮልናል ።
ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ
ኂሩት መለሰ
ነጋሽ መሀመድ