የፈረንሳይ 100ኛ ዓመት ብሔራዊ ክብረ በዓል
ዓርብ፣ ሐምሌ 7 2009«ፈረንሳይ በከፍተኛ የፀጥታ ቁጥጥር ስር ሆና በዛሬዉ ዕለት ባስትል በመባል የሚታወቀዉን የፈረንሳይ 100ኛ ብሔራዊ ቀን መታሰብያ አከበረች። የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኤማኑኤል ማክሮ በበዓሉ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙትን የዩናይትድ ስቴትስ አቻቸዉን ዶናልድ ትራምፕን አመስግነዋል። በክብረ በዓሉ ላይ ማክሮ ግልፅ በሆነ ወታደራዊ ተሽከርካሪ በፈረሰኞች ታጅበዉ ወታደራዊ ሰልፈኞቹን ጎብኝተዋል፤ ንግግርም አድርገዋል።
«የዛሬዉ ዕለት የምናከብረዉ ፈረንሳይን ነዉ፤ አንድ ያደረገንን ዕለት ነዉ የምናከብረዉ፤ ከነፃነታችን ጋር ፍፁም ትስስር ያለዉን፤ ነፃነት የምንለዉን፤ ለእያንዳንዱ ምኞት ዕድል የሚሰጠዉን፤ እኩልነት የምንለዉን፤ በዓል ነዉ የምናከብረዉ። ይህ ቁርጠኝነት ይህ ማንንም ወደ ጎን የማይተዉ ወንድማማችነት ማሳያ ነዉ።»
በፓሪሱ ሾንዘ ሊዜ ጎዳና ላይ የሀገሪቱ አርበኛ ሰልፈኞች የክብረ በዓሉ ተካፋዮች ነበሩ። ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበዓሉ ላይ የተገኙት ሀገራቸዉ ከፈረንሳይ ወገን በመቆም አንደኛዉን የዓለም ጦርነት የተቀላቀለችበት 100ኛ ዓመትን ምክንያት በማድረግ መሆኑ ታዉቋል። 3,700 ወታደሮች በበዓሉ ላይ ሰልፍ አሳይተዋል። የአሜሪካ ወታደሮችም በዚህ ሰልፍ ላይ የተሳተፉ ሲሆን አምስት ወታደሮች በአንደኛዉ የዓለም ጦርነት ወቅት የነበረ መለዮ አድርገዉ እንደነበር ተገልፆአል። ማርኮ በሰልፉ ላይ ባሰሙት ንግግር ዩናይትድ ስቴትስና ፈረንሳይ መቼም የማይለያዩ ወዳጆች ናቸዉ ሲሉ ተናግረዋል። በክብረ በዓሉ ላይ ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕንና ባለቤታቸዉ በመገኘታቸዉ አመስግነዋል።
«የዩናይድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና ባለቤታቸዉ በዚህ ክብረ በዓል ከጎናችን መገኘት ለዓመታት የዘለቀዉን ወዳጅነት ማሳያ ነዉ። ላመሰግናቸዉ እወዳለሁ። ዩናይትድ ስቴትስ ከ 100 ዓመት በፊት ላደረገችዉ ምርጫ ማመስገን እወዳለሁ። »
የሁለቱ ሃገር ፕሬዚዳንቶች እንደ ከባቢ የአየር ጥበቃ የመሰሉ ብዙ የማይስማሙባቸዉ ነጥቦች ቢኖሩም ለመቀራረብ ጥረት ሲያደርጉ መታየቱ ተዘግቦአል።
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ