1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጸጥታው ምክር ቤት እና ጀርመን

ዓርብ፣ ሰኔ 1 2010

ጀርመን የተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ጥበቃ ምክር ቤት ተዘዋዋሪ አባል ለመሆን አበክራ ስትጥር ነበር።ዛሬ ተሳካላት።የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት ከአንድ ሰዓት በፊት በሰጠዉ ድምፅ የምክር ቤቱን አምስት ተለዋጭ አባላት መርጧል። ከጀርመን በተጨማሪ በየሁለት ዓመቱ ለሚቀያየረዉ የአባልነት መቀመጫሌሎች አራት ሃገራትም ተመርጠዋል።

https://p.dw.com/p/2zBDD
USA, New York: Tag Drei:UN Wahl 2019-2020
ምስል picture-alliance/dpa/Y. Jansens

ለሁለት ዓመታት አባልነት ተመረጠች

ከጥቂት ሳምንታት በፊት ኒዉ ዮርክ በሚገኘው የተመድ ዋና መሥሪያ ቤት ተገኝተው የነበሩት የጀርመን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሃይኮ ማስ ሀገራቸው በፀጥታው ምክር ቤት ቦታ ሊኖራት ይገባል የሚል ድምጻቸውን አሰምተዋል። የጀርመንን ይህን ፍላጎትም በርካታ ሃገራት በአዎንታዊ ስሜት እንደሚደግፉታልም ሲሉ ተናግረዋል።

«በጀርመን ላይ ያለውን ከፍ ያለ መተማመን መመልከቴ አስደስቶኛል። ይህ ብቻም አይደለም ለፀጥታው ምክር ቤት አባል ለመሆን በእጩነት መቅረባችንንም ብዙዎች ደግፈውታል። የእኛን ተፅዕኖ ወደዚያ እንድናመጣ ጥያቄ ቀርቦልናል። ያንን ለማድረግ እኛም እንፈልጋለን።»

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በወቅቱ ያደረጉት ንግግር በተለይ ጀርመን በዓለም ሰላም ረገድ ቀውስን በመከላከል እና በማረጋጋት ጠቃሚ ሚና መጫወት እንደምትሻም ዘርዝረዋል። ለፀጥታውም ከፍጥጫ ይልቅ ውይይት፤ በጦር መሣሪያ ከመደራጀት ይልቅ ትጥቅ መፍታት አዎንታዊ ውጤት ያስገኛል ብላ ሀገራቸው እንደምታምንም አመልክተዋል። በየዓመቱ የተመድ ጠቅላላ ጉባኤ አዳዲስ የፀጥታው ምክር ቤት ለሁለት ዓመታት አባላነት የሚገቡ አምስት ሃገራትን ይመርጣል። ዛሬ ድርጅቱ በሚያካሂደው ስብሰባ የሚመረጡትም በመጪዉ ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት 2010 እና 2020ዓ,ም በአባልነት መቀመጫውን ይይዛሉ።  

ለምርክ ቤቱ አባልነት ከሚወዳደሩት መካከል ከአረብ ሃገራት ጋር ውዝግብ ውስጥ የገባችው እስራኤል ራሷን አግልላለች። አጋጣሚው ለጀርመን የተሻለ ዕድል ሊፈጥር እንደሚችል ቢገመትም፤ ቤልጅግም ሌላዋ ተፎካካሪ ሆና ቀርባለች። ጀርመን እንደተመኘችውም ዛሬ በተካሄደው የድምጽ አሰጣጥ ስርዓት የአባል ሃገራቱን 184 ድምፅ ስላገኘት ከሚቀጥለው ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት ጀምራ ለሁለት ዓመት የምክር ቤቱ አባልነት መንበርን ትይዛለች። ቤልጅየም፤ ደቡብ አፍሪቃ እና ዶሜኒካን ሪፑብሊክም እንዲሁም  ከእስያ ደግሞ ኢንዶኔዢያ እና ማልዲቭ በፀጥታው ምክር ቤት አባልነት የሚያስገባቸውን ድምፅ አግኝተዋል።  አምስት ቋሚ እና ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት ያላቸው አባላት እና ሌሎች አስር መደበኛ አባላት ያሉት የመንግሥታቱ ድርጅት ምክር ቤት በዓለም ወሳኝ የሚባሉ ውሳኔዎችን የሚያሳልፍ፤ ማዕቀብና ሕጋዊ ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችን የሚወስን ተቋም ነው። ከጎርጎዮሳዊዉ 2011 እስከ 2012 በምክር ቤቱ ቋሚ ያልሆነ የአባልነት መንበር የነበራት ጀርመን በሊቢያ ጉዳይ ላይ በቀረበ ረቂቅ ውሳኔ ላይ ድምጽ ባለመስጠቷ በቀሪዎቹ አባላት ትችት ደርሶባታል። ያም ቢሆን ግን ለዓለም አቀፉ የሰብዓዊ ርዳታ አቅርቦት ጠቀም ያለ ገንዘብ ከሚያዋጡት ሃገራት ሀገራቸው በአራተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ያመለከቱት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሃይኮ ማስ አሁን በምክር ቤቱ መንበር ይዘን የበኩላችንን ሚና የምንጫወትበት ጊዜ ነው በማለት ሲሟገቱ ቆይተዋል። ዛሬ ፍላጎታቸው እዉን በመሆኑ የተመድ አባል ሃገራትን አመስግነዋል።   

UN-Hauptquartier | Deutscher Außenminister Heiko Maas hält eine Rede
የውጭ ጉዳይ ሚኒኒስትር ሃይኮ ማስምስል Getty Images/AFP/H. Retamal

 

ሸዋዬ ለገሠ/ራልፍ ቦዘን

ኂሩት መለሰ