1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቀዩ ብርጌድ

ማክሰኞ፣ መጋቢት 25 2010

«ቀዩ ብርጌድ» የተባለው የጀርመኑ ግራ አክራሪ አሸባሪ ቡድን ጀርመን ውስጥ የመጀመሪያውን ጥቃት ከጣለ ትናንት 50 ዓመት ሞላው። ቡድኑ ከዛሬ 20 ዓመት በፊት የፈረሰ ቢሆንም እስካሁን መልስ ያላገኙ በርካታ ጥያቄዎች አሉ።

https://p.dw.com/p/2vQgm
Frankfurt Ausgebrannter Kaufhof 1968
ምስል picture-alliance/AP Photo/C. Hampel

ቀዩ ብርጌድ

 በጀርመንኛው ምህጻሩ ኤርአኤፍ የሚባለው ቀዩ ብርጌድ በያኔዋ ምዕራብ ጀርመን በጎርጎሮሳዊው ከ1970 ዎቹ እስከ 1990 ዎቹ መጨረሻ ልዩ ልዩ ጥቃቶችን የሚጥል ድርጅት ነበር።  በከተማ ደፈጣ ውጊያ አስተሳሰብ የተቋቋመው  ቡድኑ ምዕራብ ጀርመን ውስጥ 30 ዓመታት ለሚጠጋ ጊዜ የቦምብ ጥቃቶችን ግድያዎችን አፈናዎችን የባንክ ዝርፊያዎች ን ሲያካሂድ ቆይቷል። አውሮፕላንም ጠልፏል። በጎርጎሮሳዊው 1970 የተመሰረተው ይህ ቡድን በምዕራብ ጀርመን መንግሥት በአሸባሪነት የተፈረጀ ነው።ቡድኑ ከጎርጎሮሳዊው 1970 አንስቶ መፍረሱ እስከተነገገረበት እስከ 1998 ድረስ በጣላቸው ጥቃቶች 33 ሰዎች ሲገደሉ ከ200 በላይ ደግሞ ቆስለዋል። የተማሪዎችን እንቅስቃሴ መሠረት ያደረገው የዚህ ቡድን አርማ ቀይ ኮከብ እና ክላሺንኮቭ ጠመንጃ ነበር። ዓላማውም ያኔ ከላቲን አሜሪካ እስከ አፍሪቃ እና እስያ በተማሪዎች ይስተጋባ የነበረውን ሠራተኛውን ለሥልጣን ባለቤትነት ማብቃት እውን ማድረግ ነበር። 
ይህን ዓላማ ይዞ የተመሰረተው ቡድኑ የመጀመሪያውን ጥቃት የጣለው በጎርጎሮሳዊው ሚያዚያ 2 1968 ዓም ነው። ጥቃቱም መነሻ ያደረገው የያኔው የኢራን ሻህ በርሊንን በጎበኙበት ወቅት ለመጀመሪያ ጊዜ ለተቃውሞ አደባባይ ከወጡ ወጣቶች መካከል አንዱ፣ በፓሊስ ጥይት ተመትቶ መገደሉ ነው። የወጣቱ መገደል ብዙዎችን ለበለጠ ተቃውሞ አነሳሳ። ወጣቱ ከተገደለ በኋላ ብርጌዱ ፍራንክፈርት ውስጥ የሚገኙ ሁለት ሱቆችን በእሳት አጋየ። ይህ የመጀመሪያው ጥቃት ነበር። 
በዚህ አንድ ያለው ቀዩ ብርጌድ ሰዎችን መግደል እና ማፈኑን አጠናክሮ አውሮፕላን እስከ መጥለፍ ደረሰ ።ቡድኑ የተመሰረበት ዓላማ እና አነሳሱ ቢታወቅም እንዴት መጠናከር እንደቻለ እንዲሁም እስካሁን ስላልተያዙት የቀድሞ አባላት ያሉት መረጃዎች የተድበሰበሱ መሆናቸው ነው የሚነገረው። ይሁን እና ስለ ቡድኑ በየጊዜው የተጻፉ መጸሀፍት እና የተሰሩ ፊልሞች እንዲሁም ተመራማሪዎች ፧አንዳንዶቹን መረጃዎች ይፋ እያደረጉ ሄደዋል። መቀመጫቸውን ሰሜን ጀርመን ሀምቡርግ ያደረጉት ቮልፍጋንግ ክራውሻር የተባሉ የፖለቲካ ሳይንስ ምሁር እንደሚሉት መሠረቱን የተማሪዎች ተቃውሞ ባደረገው በዚህ ቡድን እንቅስቃሴ ውስጥ ፔተር ኡርባህ የተባለ የጀርመን ስለላ ድርጅት ባላደረባ ቁልፍ ሚና አለው። ግለሰቡ ለሰልፈኞች ጓዳ ሰራሽ ፈንጂ ማከፋፈል ብቻ ሳይሆን ፈንጂው የታሰበለትን ዓላማ ሊያሳካ የሚችልበትን መንገድ በመሳየት ጭምር ያግዝ እንደነበር ገልጸዋል። 
« ኡርባህ  እጅግ ለተቆጡ እና ለተናደዱ ሰልፈኞች ያከፋፈላቸውን ጓዳ ሰራሽ ፈንጂዎች የሚይዝበት ዘንቢል ነበረው። እነዚህ ጓዳ ሰራሽ ፈንጂዎች የታሰበላቸውን ዓላማ ማሳካት ሳይችሉ ሲቀሩ ኡርባህ መኪናዎችን እንዴት ማቃጠል እንደሚችሉ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ያሳያቸው ነበር። »
መሀላቸው ሆኖ እነርሱን ይሰልል የነበረው ኡርባህ ጓዳ ሰራሽ ፈንጂዎችን ብቻ ሳይሆን ሽጉጥም አከፋፍሏቸው እንደነበር ነው መረጃዎች የሚጠቁሙት ። ይልማ ኃይለ ሚካኤል
ይሁን እና ክራውሸር እንዳሉት መንግሥትም ሆነ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ያኔ ስለሆነው አሁንም በግልጽ መናገር አለመቻላቸው ከግማሽ ምዕተ ዓመት በኋላ እንደ አንድ ድክመት ይታያል። ኡርባህ በሰራቸው ሥራዎች ብርጌዱ ጥቃት ወደሚጥል ቡድንነት እንዲቀየር አድርጓል ብሎም አፍን ሞልቶ ለመናገር ያዳግታል ያሉት ክራውሸር ሆኖም ቁልፍ ሚና መጫወቱ አይካድም ብለዋል። ክራውሸር ለስለላ የተላከ ሰው እንዲህ ዓይነት ድርጊት እንዲፈጽም የማድረጉ ምክንያቱ ምን ሊሆን ይችላል ? ። ለሚለው ጥያቄ  የበኩላቸውን ግምት ሰንዝረዋል።
«ጥያቄው ምን ታስቦ ነው ይህ የተደረገው? ነው ። በኔ አስተያየት ኃይል የሚጠቀሙ ተቃዋሚ ሰልፈኞች ወይም ተቃዋሚዎች ብሎም የግራ ክንፍ ንቅናቄዎች በሚወስዱት የኃይል እርምጃ በራሳቸው ድርጊት ተዓማኒነታቸውን እንዲያጡ ለማድረግ ነው። » 
ከቡድኑ አባላት መካከል የታሰሩ የራሳቸውንም ህይወት ያጠፉ አሉ። ሦስት አባላቱ ግን እስካሁን አልተያዙም። የጀርመን ፌደራል የወንጀል ምርመራ ፖሊስ ከ1990 ዎቹ አንስቶ የተሰወሩትን የሦስቱን ተፈላጊዎች የቅርብ ጊዜ ፎቶዎች ባለፈው ህዳር ይፋ አድርጓል። ይህን ማድረግ የቻለውም የተፈላጊዎቹን የቅርብ ጊዜ እንቅስቃሴ ከጠቆሙ መረጃዎች በመነሳት ነበር።ይልማ
የጀርመኑ የግራ አክራሪ አሸባሪ ቡድን አባላት በሦስት የትውልድ ዘመን ይከፋፈላሉ። የመጀመሪያው ትውልድ የሚባሉት መሥራቾቹ ናቸው። ሁለተኛ ትውልድ የሚባሉት ደግሞ  የመጀመሪያው ትውልድ ከታሰረ በኋላ በ1972 የተተኩት ናቸው ነው። ሦስተኛው ትውልድ የሚባለው ደግሞ ከ1980 ዎቹ እና 90 ዎቹ እስከ 1998 ከቡድኑ ጋር የዘለቁት አባላት ናቸው። ሥስተኛው ትውልድ ቡድኑ መፍረሱን በጎርጎሮሳዊው ሚያዚያ 20 1998 ለሮይተርስ ዜና ወኪል በፋክስ በላከው የድርጅቱን ዓርማ በያዘ ደብዳቤ አሳውቋል። ይሁን እና ቡድኑ ፈረሰ ከተባለ በኋላም በተለያዩ ዓመታት በተፈጸሙ ዝርፊያዎች የቡድኑ አባላት መሳተፋቸውን የሚያመለክቱ ማስረጃዎች ተገኝተዋል። እነዚህ ዝርፊያዎች ግን ገንዘብ ለማግኘት ከመካሄዳቸው ውጭ የፖለቲካ ዓላማ እንደሌላቸው ነው የተነገረው። በጀርመን ታሪክ ጠባሳ ጥሎ ባለፈው የቀዩ ብርጌድ የሦስት አሥርት ዓመታት እንቅስቃሴ የ34 ሰዎች ህይወት ጠፍቷል። 24 አባላቱም ሞተዋል። ቤተሰቦች ተበትነዋል ልጆች ካለወላጅ እንዲያድጉ ሆኗል። 

Fahndung nach Ex-RAF-Terroristen Burkhard Garweg Volker Staub
ምስል picture-alliance/dpa/Staatsanwaltschaft Verden
Deutschland Fahndung Ex-RAF Terroristen
ምስል picture-alliance/dpa/Landeskriminalamt Niedersachsen
Lufthansa Landshut 1977 - 2017
ምስል picture-alliance/AP Photo/H. Koundakjian
Deutschland - Polizeibeamte stehen am Wrack der Herrhausen-Limousine in Bad Homburg 1989
ምስል picture-alliance/dpa/K.U. Wärner

ኂሩት መለሰ

አርያም ተክሌ