1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዓባይ ግድብ፤ ኢትዮጵያ ሱዳን እና ግብፅ

ዓርብ፣ መጋቢት 14 2010

«አንደኛዉ መታወቅ ያለበት ከህዳሴ ግድብ ጋር በተያያዘ ድርድር ሳይሆን ዉይይት ነዉ እየተካሄደ ያለዉ። ዉይይቱ በካርቱም መጋቢት 26 እና መጋቢት 27 ነዉ የሚካሄደዉ። »

https://p.dw.com/p/2unl8
የኢትዮጵያ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ መለስ ዓለም
የኢትዮጵያ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ መለስ ዓለም ምስል DW/G. Tedla

«ኢትዮጵያ ሱዳንና ግብፅ መጋቢት 26 እና 27 ካርቱም ላይ ለዉይይት ይቀመጣሉ»

በሳምንቱ መጀመርያ ካይሮ ውስጥ የተነጋገሩት የሱዳን ፕሬዝዳንት ኦማር ኧል በሽር እና የግብጽ ፕሬዝዳንት አብደል ፈታህ ኧልሲሲ፣ ስለ አባይ ግድብ ሲካሄድ የቆየው ንግግር እንዲቀጥል ከኢትዮጵያ ጋር ለመስራት መስማማታቸውን አስታውቀዋል። መሪዎቹ ጉዳዩን የተመለከተ ዝርዝር መግለጫ ግን ኧልሰጡም። ስለ ሁለቱ መሪዎች ንግግር ዶቼቬለ የኢትዮጵያ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን አስተያየት ጠይቋል።

ሱዳን በካይሮ የሚገኙትን አምባሳደርዋን ለምክክር ከጠራችና ሁለቱ ሃገሮች የዲፕሎማሲ ዉዝግብ ላይ መሆናቸዉ እየተሰማ ባለበት ወቅት የሱዳኑ ፕሬዝደንት ኦማር ኧልበሽር ከግብፅ አቻቸዉ ጋር ለመነጋገር ካይሮ የገቡት በሳምንቱ መጀመርያ ሰኞ ነበር። ፕሬዝደንት አብደል ፈታህ ኧል ሲሲ ኧልበሽርን በካይሮ አዉሮፕላን ማረፊያ ተገኝተዉ ነው የተቀበሏቸው። የጋራ መግለጫ መስጠታቸዉም ተመልክቷል። ከዚህ ቀደም በአባይ  ወንዝ ላይ የኃይል ማመንጫ ግድብ የምትገነባዉን ኢትዮጵያን ትደግፋለች በሚል ሱዳን ከግብጽ ወቀሳ ይቀርብባት ነበር። ሁለቱ ሃገሮችም ሀላያብ በተባለው ግዛት ምክንያት ዘለግ ላለ ጊዜ ሲወዛገቡ ቆይተዋል። የኧልባሽር የግብፅ ጉብኝት ኢትዮጵያ ግብጽ እና ሱዳን በአባይ ወንዝ ላይ ስለሚሰራው ግድብ በሚያደርጉት ቀጣይ ዉይይት ላይ ምን ዓይነት ተጽእኖ ይኖረዉ ይሆን ለሚለዉ፤ የኢትዮጵያ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ መለስ ዓለም፣

Äthiopien Grand Renaissance Staudamm
ምስል Reuters/T. Negeri

«ጉብኝቱን የወሰኑት ሁለቱ ሃገሮች ናቸዉ። በሁለቱ ሃገር መካከል ያለ ግንኙነት እንዴት መከናወንና እንዴት መሄድ አለበት የሚለዉን እኛ ልወስን አንችልም። አንደኛ ይህ መታወቅ ይኖርበታል። ሁለተኛ አባይና ሕዳሴ ግድብ ጋር በተያያዘ የሚደረግ ዉይይት የሦስትዮሽ ዉይይት ነዉ። የዚህ ጉብኝት አላማ እነሱም በመገናኛ ብዙኃን በግልፅ እንዳስቀመጡት በሁለቱ ሃገሮች መካከል ተፈጥሮ የነበረዉን አለመግባባት ለማስወገድ ለማስቀረት የተደረገ ጉብኝት ነዉ። በሁለቱ ሃገሮች መካከል የሚኖር ሰላማዊ ግንኙነት ለኛም ጠቃሚ ነዉ ብሎ መዉሰድ ይቻላል።»   

በአባይ አጠጠቃም ጉዳይ ላይ ሦስቱ ሃገሮች ማለት ኢትዮጵያ ሱዳን እና ግብፅ በመጭዉ መጋቢት 26 እና መጋቢት 27 ካርቱም ላይ ለዉይይት ይቀመጣሉ ያሉት አቶ መለስ፤ በአባይ ግድብ ላይ ዉይይት እንጂ ድርድር የለም ሲሉ አፅኖት ሰጥተው ተናግረዋል።

« አንደኛዉ መታወቅ ያለበት ከህዳሴ ግድብ ጋር በተያያዘ ድርድር ሳይሆን ዉይይት ነዉ እየተካሄደ ያለዉ። ዉይይቱ በካርቱም መጋቢት 26 እና መጋቢት 27 ነዉ የሚካሄደዉ። ይህ ዉይይት የተወሰነዉ አዲስ አበባ ላይ የአፍሪቃ ኅብረት ስብሰባ በተካሄደበት ወቅት የኢትዮጵያ ሱዳንና ግብፅ መሪዎች አዲስ አበባ ላይ ተገናኝተዉ ለዉጭ ጉዳይ ሚኒስትሮቻቸዉ የሰጡት ኃላፊነት ነበር። ሚኒስትሮቹ በአንድ ወር ዉስጥ ተገናኝተዉ ከሕዳሴ ግድብ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ያልተፈቱ ጉዳዮች ን መርምረዉ የመፍትሄ ሃሳብ ለማቅረብ የወሰኑበት ስብሰባ ነዉ። ስለዚህ ዉይይቱ ካርቱም ላይ ይካሄዳል። ሌላዉ ድርድር አይደለም ያልኩበት ምክንያት የህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያ ሕዝብ የረጅም ጊዜ ህልም በመሆኑና ያንን ሕልም ነዉ እዉን እያደረጉ ያሉት። 45% የሚሆነዉ አካባቢ የሚኖረዉ በዚሁ አካባቢ ነዉ። ከገጠሩ አካቢ ስድስቱ በዚሁ ተፋሰስ አካባቢ የሚኖር ነዉ። ኢትዮጵያ ዉስጥ 65 ሚሊዮን ሕዝብ ጨለማ ዉስጥ ነዉ የሚኖረዉ፤ መብራት አያገኝም። በእንደዚህ ሁኔታ ላይ እያለን የሕዳሴ ግድብ ይሰራ አይሰራ የሚል ድርድር ዉስጥ አይደለም የምንገባዉ። የሕዳሴ ግድብ መሪት ላይ የሚታይ ሃቅ ሆንዋል። በአጠቃላይ ግን የዚህ ፕሮጀክት አፈፃፀም ከኢትዮጵያ አልፎ ግብፅና ሱዳንን አልፎ ለሌሎች የአካባቢ ሃገሮችን የሚጠቅም ነዉ ብለን ስለምናምን በበጎ አመለካከት እየተካሄደ ያለ ዉይይት እንጂ ድርድር አይደለም» የኢትዮጵያ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ መለስ ዓለም «የሱዳን እና የግብፅ ዲፕሎማስያዊ ግንኙነት መሻሻል ላይ በሰጡት አስተያየት የጎረቤቶቻችን ሰላም የኛም ሰላም ነው» ብለዋል።

Sudan Khartum Abkommen gemeinsame Nil-Wasser Nutzung
ምስል AP Photo/Mohammed Abd el-Moaty, Egyptian Presidency

አዜብ ታደሰ

ኂሩት መለሠ