1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

 የሮሒንጃያዎች መከራ

ዓርብ፣ መስከረም 5 2010

በመታሰር፤ መገፋት፤ መንገላታታቸዉ ዓለም የጮኸ፤የታገለ፤ ምርጥ የሠላም ሽልማቱን የሰጣቸዉ የምያንማር መንግሥት ተዘዋዋሪ መሪ ኦዉንግ ሳን ሱ ቺ ግድያ ግፍ በደሉን ያስቆማሉ የሚል ተስፋ ነበር።የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬሽ በሁለት ሳምንት ዉስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ትናንት በሰጡት መግለጫ  ተስፋዉ በንኖ ግፉ ማየሉን አረጋገጡ።

https://p.dw.com/p/2k03z
Rohingya Krise in Bangladesch
ምስል DW/M.M. Rahman

ጩኸት ማስጠንቀቂያዉ ቀጥሏል።ግፉም

የምያንማር መንግስት በሮሒንጃያ ሙስሊሞች ላይ የሚያፈፅመዉን ግፍ በአቸኳይ እንዲያቆም የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት አሳሰበ።የአዉሮጳ ሕብረት ሕብረት እና የተለያዩ መንግስታትም የምያንማር መንግሥት የሚፈፅመዉን ግድያ እና በደል አዉግዘዋል።የአዉሮጳ ሕብረት የምክር ቤት እንደራሴዎች ሕብረቱ ከዚሕ ቀደም ለምያንማርዋ መሪ የሰጠዉን የሳኻሮቭ ሽልማት መመለስ የሚቻልበት መንገድ እንዲፈለግ ጠይቀዋል።የምያንማር ጦር ሠራዊት የሚያደርስባቸዉን ግፍ ሸሽተዉ ባንግላዴሽ የገቡት የሮሒንጃያ ሙስሊሞች ቁጥር ወደ 400 ሺሕ ደርሷል።ነጋሽ መሐመድ ዝርዝር 

ቀን የጎደለባቸዉ-ያዩ እንደሚሉት አንድም በጥይት አለያም ከየቤታቸዉ ጋር በእሳት ጋይተዋል።በትክክል የቆጠራቸዉ የለም።ከተረፉት በሽተኞች በቃሬዛ፤ አካለ ጎደሎ፤ ደካሞች እና አዛዉንቶች የወሳሳ ተይዘዉ፤ወይም ተደግፈዉ ሕፃናት ታዝለዉ በዱር፤ ደን ጢሻዉ እየተሽሎኮሎኩ፤በወንዝ፤ ዉሐ ማጥ ድጡ እየተንቦራጨቁ፤  ይግተለተላሉ።ወደ ባንግላዴሽ።«ጦር ሠራዊቱና ፖሊስ መንደራችንን ከብበዉ በሮኬት ሲያጋዩት ከየቤታችን ወጥተን ባገኘነዉ አቅጣጫ ሸሸን።»ይላሉ አብዱል ጎፋር።የተከበሩ ያገር ሽማግሌ ነበሩ።አሁን ሩዝ ለማኝ ስደተኛ ሆነዋል።ግን እድለኛ ናቸዉ።ተርፈዋል።እንደሳቸዉ ከጥይት፤ ሮኬት፤እሳት፤ አምልጠዉ ከጀርልባ አደጋ ተርፈዉ ባንግላዴሽ የገቡት የሮሒንጃያ ሙስሊሞች ቁጥር ወደ አራት መቶ ሺሕ ደርሷል።

የምያንማር  መንግስት ጦር ከሰወስት ሳምንት በፊት የጀመረዉን ሮሒንጃያዎችን የማጥፋት ዘመቻ እንዲያቆም አለም አቀፍ ተቋሟት፤ የመብት ተሟጋች፤ ማሕበራት እና ድርጅቶች ጠይቀዋል።መንግስታት ጠንካራ ያሉትን ግፊት አድርገዋል።ሕዝብ  ከአንካራ እስከ ጃካርታ ከካራቺ እስከ ሙባይ ባደባባይ ሰልፍ ተቃዉሟል።

                                  

በመታሰር፤ መገፋት፤ መንገላታታቸዉ ዓለም የጮኸ፤የታገለ፤ ምርጥ የሠላም ሽልማቱን የሰጣቸዉ የምያንማር መንግሥት ተዘዋዋሪ መሪ ኦዉንግ ሳን ሱ ቺ ግድያ ግፍ በደሉን ያስቆማሉ የሚል ተስፋ ነበር።የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬሽ በሁለት ሳምንት ዉስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ትናንት በሰጡት መግለጫ  ተስፋዉ በንኖ ግፉ ማየሉን አረጋገጡ።«ሰብአዊ ድቀቱ እጅግ ከፍተኛ ነዉ።ባለፈዉ ሳምንት ስንገናኝ ወደ ባንግላዴሽ የሸሹት የሮሒንጃያ ስደተኞች 125 ሺሕ ነበሩ።ይሕ ቁጥር አሁን በሰወስት እጥፍ ጨምሮ 380 ሺሕ ደርሷል።»ጋዜጠኛዉ ጉተሬሽን ጠየቀ።የሚፈፀመዉን በደል የዘር ማፅዳት ማለት ይቻላል።» ብሎ።መለሱ-አንጋፋዉ ዲፕሎማት ጥያቄዉን በጥያቄ።

Rohingya Krise in Bangladesch
ምስል DW/M.M. Rahman

                               

«ጥያቄሕን በሌላ ጥያቄ ልመልስ፤ከሮሒንጃያ ሕዝብ አንድ ሰወስተኛዉ እየተሰደደ፤ ሌላ ቃል ታገኝለታለሕ።»ሳን ሱ ቺ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት እና ከዓለም አቀፍ የመብት ተሟጋች ድርጅቶች የሚሰነዘርባቸዉን ትችት በመቃወም ሰሞኑን በሚደረገዉ የድርጅቱ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ አልካፈልም ብለዋል።ትናንት የተሰየመዉ የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት የሳንሱቺን ኩርፊያ ርዕሱ አላደረገዉም።የምክር ቤቱ የወቅቱ ፕሬዝደንት ኢትዮጵያዊዉ ዲፕሎማት ዶከተር ተቀዳ አለሙ በንባብ ያሰሙት መግለጫ በሰላማዊ ሰዎች ላይ የሚፈፀመዉን ግድያና ግፉ አዉግዟል።

                                

«የፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት አባላት የምያንማር ፀጥታ አስከባሪዎች በሚያደርጉት የፀጥታ ዘመቻ አለቅጥ የበዛ ጥፋት መድረሱ በጣም አሳስቧቸዋል።በራኺነ ግዛት ያለዉ የኃይል እርምጃ ባስቸኳይ እንዲቆም፤ ሁኔታዉ እንዲረጋጋ፤ ሕግ እና ሥርዓት እንዲከበር ጠይቀዋል።ሰላማዊ ሰዎች ጥበቃ እንዲደረግላቸዉ፤ የማሕበረ-ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲመለሱ እና የስደተኞቹ ቀዉስ እንዲፈታ አሳስበዋል።»

ጠንካራ ዉግዘት የተሰማዉ ከአዉሮጳ ሕብረት ነዉ።ሽትራስቡርግ-ፈረንሳይ ዉስጥ የተሰበሰቡት የሕብረቱ የምክር ቤት እንደራሴዎች እንዳሉት ኦዉንግ ሳን ሱ ቺ የጎሳና እና የሐይማኖት ጥላቻን የሚያቀጣጥሉ እርምጃዎችን በሙሉ ማዉገዝና ለማስቆም መጣር አለባቸዉ።ምክር ቤቱ እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር  በ1990 ለወይዘሮ ሳን ሱ ቺ በሳኻሮቭ ሥም የተሰየመዉን ታላቅ ሽልማቱን ሸልማቸዋል።እንደራሴዎቹ እንደሚሉት ሳንሱ ቺ በሮሒንጃያ ሙስሊሞች ላይ የሚደርሰዉን በደል ካላስቆሙ ሽልማቱን ሊቀሙ ይገባል።ምክንያቱም ሽልማቱ ሰብአዊ መብትን ለሚያስከብር እንጂ ሰብአዊ መብትን ለሚረግጥ አይሰጥምና።

Rohingya Krise in Bangladesch
ምስል DW/M.M. Rahman

ነጋሽ መሐመድ

ኂሩት መለሰ